ቀጥታ, ፕሬዝዳንት ትራምፕ በሩሲያ እና በኢራን ላይ ማዕቀብ የሚጥል ረቂቅ ላይ ፈረሙ

የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የሩሲያ የነዳጅ እና ጋዝ አቅርቦት ላይ ያነጣጠረ ማዕቀብ ተግባራዊ እንዲሆን ፊርማቸውን አኖሩ። ትራምፕ የፈረሙበት ረቂቅ ከሩሲያ ጋር ትስስር ያላት ኢራን ላይ የተጣሉ ማዕቀቦችን ዘላቂ የሚያደርግም ነው።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ደቡብ አፍሪካውያን በጆሃንስበርግ ተገድለው የተገኙትን ዘጠኝ ሴቶች ለመዘከር እና መፍትሔ ለመጠየቅ ተሰባሰቡ

    ሟቾቹን ለማሰብ እና መፍትሔ ለመጠየቅ የተሰባሰቡ ደቡብ አፍሪካውያን። አንዲት ሴት 'አትግደሉን' የሚል መፈክር ይዛለች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ደቡብ አፍሪካውያን በዚህ ሳምንት በጆሃንስበርግ አቅራቢያ ተገድለው የተገኙትን ዘጠኝ ሴቶች ለመዘከር እና መፍትሔ ለመጠየቅ ተሰባሰቡ።

    በርካቶች ሴቶች በየቀኑ የሚጋፈጡት እንደሆነ የሚገልጹት ጥቃት ቁጣ እና ስጋትን ፈጥሯል።

    ሮይተርስ እንደዘገበው ባለፉት ሁለት ወራት ፖሊስ በምሥራቃዊ ጆሃንስበርግ ኢኩርሁልኒ የዘጠኝ ሴቶችን አስክሬን ያገኘ ሲሆን ምርመራ እያካሄደ ነው።

    አብዛኞቹ ሟቾች በ20ዎቹ እና በ30ዎቹ የዕድሜ ክልል የሚገኙ ናቸው። አንዳንዶቹ ልብሶቻቸው የተቀዳደዱ ሲሆን ወሲባዊ ጥቃት እንደተፈፀመባቸው የሚያሳዩ ምልክቶች ታይተውባቸዋል።

    በጆሃንሰበርግ ከተገደሉት መካከል አንዷ የሆነችውን ኤሊዛቤት ሞስላክጎሞ የመታሰቢያ ሥነ ሥርዓት ዛሬ እየተካሄደ ነው።

    ኤሊዛቤት ለመሮጥ ከቤቷ ከወጣች በኋላ ነበር ከቀናት በኋላ አስክሬኗ የተገኘው።

    ሀዘንተኞች ሻማ በማብራት እና “በቃ! በሴቶች ላይ የሚፈፀም ግድያ ይቁም” የሚሉ መፈክሮችን ይዘው ታይተዋል።

    ጥቁር ለብሰው በመታሰቢያ ሥነ ሥርዓቱ ላይ ከተገኙት መካከል ሊራቶ ሊንትሴላ የተባለች ሴት “እዚህ የተገኘነው ኤልዛቤትን ስላጣን ነው። ግን እኛም የትም ቦታ ደኅንነታችን የተጠበቀ አይደለም” ብላለች።

    ግድያዎቹ እአአ በ2025 ፆታን መሠርት ያደረጉ ጥቃቶች ብሔራዊ ቀውስ ሆኖ በታወጀባት ደቡብ አፍሪካ ቁጣን ቀስቅሷል።

    በርካታ ሴቶች ለጥቃቱ የተሰጠው ትኩረት እና የባለሥልጣናት ቃል ደኅንነት እንዲሰማን ማድረግ አልቻለም ብለዋል፥።

    ፕሬዚደንት ሲሪል ራማፎዛ ሐሙስ ዕለት ደቡብ አፍሪካ እንዲህ ዓይነቱን ጥቃት እንድትለምድ እንማይፈቅዱ እና ድርጊቱን ፈፃሚዎች ለፍርድ እንደማያቀርቡ ቃል ገብተዋል።

    ነገር ግን የደቡብ አፍሪካ ፖሊስ አገልግሎት በሙስና እና በበጀት እጥረት ተዳክሟል። በዚህም ምክንያት ከ10 ግድያዎች ውስጥ ምርመራ ተደርጎ ለፍርድ የሚቀርበው አንዱ ብቻ ነው።

    ደቡብ አፍሪካ ከፍተኛ ጾታን መሠረት ያደረጉ ጥቃቶች ከሚፈጸምባቸው አገራት መካከል አንዷ ስትሆን በአማካኝ በዓለም ላይ ከሚገደሉ ሴቶች መካከል በአገሪቱ የሚገደሉት አምስት እጥፍ እንደሚበልጥ የተባበሩት መንግሥታት የሴቶች ድርጅት መረጃ ያሳያል።

  2. ከሁቲዎች ጋር የሚደረገው ውጊያ ከተባባሰ ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ በሪያድ የማስጠንቀቂያ ደወሎች ተሰሙ

    የሳዑዲ መዲና ሪያድ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በሳዑዲ አረቢያ መዲና ሪያድ የቅድመ ማስጠንቀቂያ እና የአደጋ ጊዜ ደወሎች መሰማታቸውን የሳዑዲ የሲቪል መከላከያ ድርጅት ገለጸ።

    በአገሪቱ እና በየመን ሁቲዎች መካከል የተፈጠረው ግጭት ከተባባሰ ወዲህ በመዲናዋ የማስጠንቀቂያ ደወሎች ሲሰሙ ይህ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው።

    የዜና ወኪሎችም በሪያድ ቢያንስ ሁለት ፍንዳታዎች መስማታቸውን ዘግበዋል።

    ማስጠንቀቂያው የተሰማው የሁቲ ወታደራዊ ቃል አቀባይ በሰንዓ ተፈፀመ ያሉትን እና ሳዑዲ አረቢያን ተጠያቂ ያደረጉበትን “ የወንጀል ድርጊቶች” ማክሸፋቸውን አስታውቀው፣ ለድርጊቷ ምላሽ እንደሚሰጥ ከዛቱ በኋላ ነው።

    የሳዑዲ የሲቪል መከላከያ ድርጅት ቅዳሜ ጠዋት በአካባቢው ያለው ሁኔታ ወደ መደበኛ መመለሱን ገልጿል።

    ሕዝብ የሚበዛበትን አብዛኛውን የየመን ሰሜናዊ አካባቢዎችን ተቆጣጥረው የሚገኙት ሁቲዎች በቀይ ባሕር የሳዑዲ መርከቦችን ዒላማ በማድረግ ጥቃት ከፍተዋል።

    ሁቲዎች ከባለፈው ሳምንት ጀምሮ በፍጥነት እየገሰገሱ ሲሆን የየመንን የቀይ ባሕር ዳርቻዎችን በሙሉ ተቆጣጥረዋል።

    ይህንንም ተከትሎ ሰሞኑን የሳዑዲ አየር ኃይል በአካባቢው ላይ በመቶዎች የሚቆጠሩ የአየር ድብደባዎች መፈፀሙን ገልጸዋል። ባለፉት 24 ሰዓታት ብቻ 26 ጥቃቶችን ፈፅማለች ብለዋል ሁቲዎች።

    የአርብ ዕለቱን ጥቃት ጨምሮ ባለፈው ሳምንት ብቻ ሳዑዲ የፈፀመችው ጥቃት 300 መድረሱንም ታጣቂ ቡድኑ አስታውቋል። እነዚህ ጥቃቶች ዒላማ ያደረጉት በየመን ሁቲ የሚቆጣጠራቸውን ቦታዎች እንደሆነም ገልጿል።

    እአአ በ2014 በየመን የተቀሰቀሰው ጦርነት በ2022 በታጣቂ ቡድኑ እና በሳዑዲ መካከል በተደረሰ የተኩስ አቁም ስምምነት ጋብ ብሎ ቢቆይም ሐምሌ ወር ላይ እንደገና አገርሽቷል።

  3. የኡበር ሹፌር ተሳፋሪዋን አውራ ጎዳና ላይ አውርዶ ለኅልፈት በመዳረጉ ኩባንያው 40 ሚሊዮን ዶላር እንዲከፍል ተወሰነ

    ኤምሊ ኖርማንዲን-ፓርከር

    የፎቶው ባለመብት, Panish, Shea, Ravipudi

    በካሊፎርኒያ፣ የኡበር ሹፌር የ23 ዓመት ሴትን አውራ ጎዳና ላይ ከመኪናው አውርዶ ለኅልፈት በመዳረጉ ኩባንያው 40 ሚሊዮን ዶላር እንዲከፍል ተወሰነ።

    አሽከርካሪው አውራ ጎዳና ላይ መኪናውን አቁሞ ተሳፋሪዋ ኤምሊ ኖርማንዲን-ፓርከር እንድትወርድ ማስገደዱ ተገልጿል።

    ከጓደኞቿ ጋር ኡበር ጠርታ ወደ ቤት እየሄደች የነበረችው ኤምሊ ከመኪናው ከወረደች በኋላ በሌላ ተሽከርካሪ ተገጭታ ሕይወቷ አልፏል።

    ቤተሰቦቿ እንደተናገሩት ኤምሊ አልኮል ጠጥታ ነበር። ጓደኛዋ መኪና ውስጥ ሳለች በመታመሟ ሲያስመልሳት እንደነበርም የፍርድ ቤት ሰነዶች ያሳያሉ።

    አሽከርካሪው በግሉ የሚሠራ ተቀጣሪ ስለሆነ ኡበር ኃላፊነት እንደማይወስድ በመግለጽ በፍርድ ቤት ተከራክሯል።

    የኤምሊ ቤተሰቦች በሰጡት መግለጫ “ኤምሊ የሚጠበቅባትን አድርጋለች። ኡበር ቤቷ በሰላም እንደሚያመጣት አምና ነበር። ነገር ግን ሕይወቷን አጥታለች” ብለዋል።

    ለአምስት ቀናት የኤምሊ ቤተሰቦች እና ኡበር ከተደራደሩ በኋላ ዳኛ ሪቻርድ ስቶን ኩባንያው በገንዘብ እንዲቀጣ ወስነዋል።

  4. ትራምፕ ሲኤንኤን እና ፖሊቲኮ ዋይት ሃውስ እንዳይገቡ እንደሚያግዱ አስታወቁ

    ጋዜጠኞች በኦቫል ጽሕፈት ቤት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ትራምፕ ይህን ካስታወቁ በኋላ በኦቫል ጽሕፈት ቤት በሰጡት መግለጫ ላይ የፖለቲኮ እና የሲኤንኤን ጋዜጠኞች ነበሩ

    የአሜሪካው ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ ሲኤንኤን፣ ኤምኤስ ናው እና ፖሊቲኮ ዋይት ሃውስ እንዳይገቡ እንደሚያግዱ አስታወቁ።

    ይህም ትራምፕ ከመገናኛ ብዙኃኖቹ ጋር ባላቸው የሻከረ ግንኙነት የሰነዘሩት የቅርብ ጊዜ ዛቻ ነው።

    ፕሬዚደንቱ አርብ ዕለት በትሩዝ ሶሻል የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ መገናኛ ብዙኃኑ ስለ አስተዳደራቸው “ሁልጊዜ ፈጠራ ወይም ውሸት ይጽፋሉ፤ ይዘግባሉ” ሲሉ ከስሰዋል። ሆኖም ትራምፕ ለዚህ ክሳቸው ያቀረቡት ማሳያ የለም።

    ትራምፕ በኋላ ላይም እርምጃውን “በጣም ቀላል ገደብ” ያሉት ሲሆን እንዴት ተግባራዊ እንደሚሆን ግን ዝርዝር መረጃ አልሰጡም። የሚዲያዎቹ ሰራተኞች በአጠቃላይ ወደ ዋይት ሃውስ እንዳይገቡ ይከለክል እንደሆነም ግልጽ አይደለም።

    ሲኤንኤን ለእርምጃው ወዲያውኑ ምላሽ የሰጠ ሲሆን በአሜሪካ የፕሬስ ነፃነት ላይ የተፈፀመ “ሕገ ወጥ ጥቃት” ብሎታል።

    ፖለቲኮም መግለጫ አውጥቷል። በመግለጫው በዋይት ሃውስም ሆነ በቀጣይ ሥራዎቹ ሚዛናዊ ዘገባዎችን ማቅረብ እንደሚቀጥል ገልጿል።

    በቀድሞ ስሙ ኤምኤስኤንቢሲ እና የአሁኑ ኤምኤስ ናው ግን አስተያየት ለመስጠት አልፈቀደም።

    ትራምፕ እርምጃው ካስታወቁ በኋላ በኦቫል ጽሕፈት ቤት በሰጡት መግለጫ ላይ የፖለቲኮ እና የሲኤንኤን ጋዜጠኞች ዋይት ሃውስ ነበሩ።

    በመግለጫቸው “መገናኛ ብዙኃን ስለአሜሪካው ፕሬዚደንት፣ የትራምፕ አስተዳደር ወይም ስለአሜሪካ ሲዘግቡ ያለማቋረጥ የፈጠራ ወሬ እና ውሸት መጻፍ አይችሉም። . . . ሌሎች ሚዲያዎችም ይከተላሉ” ብለዋል።

    ሌሎች ሚዲያዎችም ይከተላሉ ማለት ምን ማለታቸው እንደሆነ ከአንድ ጋዜጠኛ ለቀረበላቸው ጥያቄም ከሐሰተኛ ዜና ጋር በተያያዘ በሌሎችም ላይ ተመሳሳይ እርምጃ ሊወሰድ እንደሚችል ጠቁመው፣ "ታውቃለችሁ፣ ኒው ዮርክ ታይምስ ሐሰተኛ ነው፣ ዋሽንግተን ፖስት ሐሰተኛ ዜና ነው የሚያሰራጨው” ሲሉ መልሰዋል።

    የፕሬዚደንቱን እርምጃ ተከትሎ የዋይት ሃውስ ዘጋቢዎች ማኅበር ፕሬዚደንት እና የፎክስ ኒውስ ዘጋቢው ጃኪ ሄንሪች ሥራቸውን በመስራታቸው ብቻ ተለይተው የተጠቀሱትን ባልደረቦቻቸውን ለመከላከል ከጎናቸው እንደሚቆሙ ተናግረዋል።

    የትራምፕ እርምጃም ሕጋዊ ተግዳሮቶች ሊገጥሙት ይችላሉ።

    ትራምፕ ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ በተደጋጋሚ መገናኛ ብዙኃንን በሐሰተኛ መረጃ የሚከሱ ሲሆን እንዲዘጉ ያደረጓቸውም አሉ።

  5. ትራምፕ በሩሲያ እና በኢራን ላይ ማዕቀብ ለመጣል የሚያስችል ረቂቅ ላይ ፊርማቸውን አኖሩ

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የሩሲያ የነዳጅ እና የጋዝ አቅርቦት ላይ ያነጣጠረ ማዕቀብ ተግባራዊ እንዲሆን ፊርማቸውን አኖሩ።

    ማዕቀቡ የሩሲያን ምጣኔ ሃብት የሚያዳክም ይሆናል።

    ማዕቀቡ እንዲጣል የቀረበው ረቂቅ ባለፈው ሳምንት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከጸደቀ በኋላ ነው ትራምፕ ፊርማቸውን ያኖሩት።

    ከሩሲያ ጋር ትስስር ያላት ኢራን ላይ የተጣሉ ማዕቀቦችን ዘላቂ ማድረግም የረቂቁ አካል ነው።

    በዚህም እንደ ቻይና እና ሕንድ ያሉ ከሩሲያ ነዳጅ እና ጋዝ የሚገዙ አገራት ላይ ትራምፕ 100% ታሪፍ መጣል ይችላሉ።

    ማዕቀቡ የኢራን የኢነርጂ እና የጦር መሣሪያ ምርት ዘርፍንም ይመለከታል።

    ከዚህ ዓለም በሞት በተለዩት የሕዝብ እንደራሴ ሊንዚ ግራሀም ስም የተሰየመው ረቂቅ 48 ገጾች አሉት።

    የሩሲያን የተፈጥሮ ጋዝ ከ15% በታች በሆነ መጠን የሚያስገቡ እና ሩሲያ ላይ ያላቸውን ጥገኝነት ለመቀነስ እየሞከሩ ያሉ አገራት በታሪፉ አይካተቱም።

    ማዕቀቡ ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲንን እና ሌሎች የሞስኮ ከፍተኛ ባለሥልጣናትን፣ ባንኮች እና የፋይናንስ ተቋማትን ያካትታል።

    ሩሲያ የተጣለባትን የነዳጅ ማዕቀብ በማለፍ ነዳጅ የምታዘዋውርባቸው መርከቦች (ሻዶ ፍሊት) ላይ ያነጣጠሩ ማዕቀቦችም ይገኙበታል።

  6. ሩሲያ በአውሮፓ ላይ የምትፈፅመው ጥቃት እየተባባሰ መምጣቱን የፈረንሳዩ ፕሬዚደንት ተናገሩ

    የፈረንሳይ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የፈረንሳይ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ሩሲያ በአውሮፓ እና በፈረንሳይ ላይ የምትሰነዝረው ወታደራዊ እና የሳይበር ጥቃትን ጨምሮ ወታደራዊ ያልሆኑ “ቅይጥ” ጥቃቶች እየተባባሱ መጥተዋል ሲሉ አስጠነቀቁ።

    ማክሮን በኤሊስ ቤተ መንግሥት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ በዚህ ስጋት ምክንያት ወሳኝ የሆኑ መሠረተ ልማቶችን እና የመከላከያ ኢንደስትሪ ቦታዎችን ለመጠበቅ እቅድ እንዲወጣ ትዕዛዝ መስጠታቸውን ተናግረዋል።

    ፈረንሳይ ባለፉት ጥቂት ሳምንታት በሩሲያ “ቅይጥ” ጥቃቶች ኢላማ ሆና እንደነበር የተናገሩት ፕሬዚደንቱ፣ ለዚህ "ምላሽ ሳይሰጥ እንደማይቀር” ገልጸዋል።

    በርካታ የአውሮፓ መሪዎችም ሩሲያ አገራቱ ዩክሬንን ለመደገፍ ምን ያህል ቁርጠኛ መሆናቸውን ለመፈተሽ ጥቃት ለመፈፀም እየተዘጋጀች ሊሆን እንደሚችል አስጠንቅቀዋል።

    የፈረንሳዩ ፕሬዚደንት ማስጠንቀቂያውን የሰጡት የመካከለኛው ምሥራቅ እና የዩክሬን ጦርነት ያስከተለው ተፅዕኖ ላይ ለመወያየት ከፓርቲ መሪዎች ጋር ስብሰባ ካደረጉ በኋላ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ነው።

    ማክሮን ባለፈው ወር በጀርመን ሌፕዚግ አየር ማረፊያ ላይ የተፈፀመውን የድሮን ጥቃት እንዲሁም የፖላንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶናልድ ተስክ ሩሲያ በፖላንድ እና በሌሎች የኔቶ አባል አገራት ላይ የድሮን እና የሚሳዔል ጥቃቶችን ለመፈፀም እያቀደች መሆኑን በመግለጽ የሰጡትን አስተያየት በማሳያነት ጠቅሰዋል።

    ባለፈው እሁድ ዕለትም የሩሲያ ድሮን በዩክሬን እና ፖላንድ ድንበር አቅራቢያ አንድ የመንገደኞች ባቡርን መትቷል። ጥቃቱ የተፈፀመው የቀድሞው የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን እና ከፍተኛ የአውሮፓ የደኅንነት ባለሥልጣናት በተመሳሳይ መስመር ካለፉ ብዙም ሳይቆይ ነበር።

    የሩሲያ ፕሬዚደንት ቭላድሚር ፑቲን በተደጋጋሚ ሩሲያ አውሮፓን የማጥቃት እቅድ እንደሌላት ተናግረዋል።

    ሆኖም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ሰርጌይ ላቭሮቭ የአውሮፓ አገራት ወደ ዩክሬን ወታደር መላክ በሩሲያ “እንደ ጦርነት እወጃ” እንደሚቆጠር በመግለጽ አስጠንቅቀዋል።

    “ አውሮፓ ሩሲያን ካጠቃች፣ ጦርነቱ የተለየ ነው የሚሆነው። በጣም አጭር ነው የሚሆነው” ብለዋል።

  7. የደቡብ ኮሪያ ፕሬዚደንት አገራቸው በኢራን ጦርነት ውስጥ ጣልቃ እንደማትገባ ተናገሩ

    የደቡብ ኮሪያ ፕሬዚደንት ሊ ጃይ ሚዩንግ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የደቡብ ኮሪያ ፕሬዚደንት ሊ ጃይ ሚዩንግ አገራቸው ከኢራን ጋር በሚደረገው ጦርነት ጣልቃ እንደማትገባ እና የጦር ኃይላቸውንም እንደማይልኩ ተናገሩ።

    ፕሬዚደንቱ ይህን ያሉት ከቅርብ ወራት ወዲህ ደቡብ ኮሪያ ከአሜሪካ ጋር በመተባበር በፋርስ ባሕረ ሰላጤ እና በሆርሙዝ ወሽመጥ መርከቦችን ከጥቃት የመጠበቅ ዘመቻን ልትቀላቀል ትችላለች የሚሉ ወሬዎች ከተናፈሱ በኋላ ነው።

    ከሁለት ሳምንት በፊትም የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ በፋርስ ባሕረ ሰላጤ እና በሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ ማንኛውም ዓይነት ተሳትፎ ወይም ወታደራዊ ስምሪት “ለእብሪተኞች ቀጥተኛ ድጋፍ እንደማድረግ እንደሚቆጠር” እና “ከፍተኛ መዘዝ እንደሚያስከትል” በመግለጽ ደቡብ ኮሪያን አስጠንቅቀው ነበር።

    ፕሬዚደንት ሚዩንግ ዛሬ አርብ መስከረም 8፣ 2019 ዓ.ም. በሰጡት መግለጫ አገራቸው በዚህ ላይ እንደማትሳተፍ እና ከኢራን ጋር በሚደረገው ጦርነት ጣልቃ እንደማትገባ አፅንኦት ሰጥተዋል።

    ጨምረውም በውጪ ጦርነት ወታደሮቻቸው እንዲሳተፉ ለመላክ በፍፁም እንደማይስማሙ አረጋግጠዋል።

    በሌላ ንግግራቸውም ፕሬዚደንቱ “ትራምፕ ንግግር እንደሚፈልጉ ግልጽ ነው፣ እናም ወደ ንግግር እንዲመጡ እኔም እጠይቃቸዋለሁ” ብለዋል።

    ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ ባለፈው ወር ደቡብ ኮሪያን እንደ አንድ የእስያ አጋር ጠቅሰው፣ በጦርነቱ አገራት እያደረጉላቸው ያለው እርዳታ “በጣም ትንሽ” እንደሆነ ተናግረዋል።

    አሜሪካ ከአገሪቱ ጋር የምታደርገውን ዓመታዊ ወታደራዊ ልምምድ የቀነሰች ሲሆን ትራምፕ ይህንን ደቡብ ኮሪያ በኢራን ጉዳይ "ትንሽም ድጋፍ ለማድረግ" ፈቃደኛ ካለመሆኗ ጋር በግልጽ አያይዘውታል።

    ከዚህም በተጨማሪ ወታደራዊ ልምምዶቹ ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቁ መሆናቸውን ገልጸው፤ ይህ ልምምዳቸው ከሰሜን ኮሪያ መሪ ኪም ጆንግ ኡን ጋር ባላቸው “በጣም መልካም ግንኙነት” ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እያሳደረ መሆኑን ተናግረዋል።

    የጋራ ወታደራዊ ልምምዱ መቀነስ እና ትራምፕ ከፒዮንግያንግ ጋር ንግግር ለመቀጠል እያደረጉት ያለው ጥረት ሴዑልን ከሰሜን ኮሪያ የኒውክሌር ፕሮግራም ድርድር ውጭ ሊያደርግ ይችላል የሚል ስጋትን ፈጥሯል።

  8. በፓኪስታን በመስጊድ ላይ በተፈፀመ ጥቃት ቢያንስ 16 ሰዎች ሞቱ

    ከጭንቅላቱ ደም እየፈሰሰ ያለ ግለሰብ በሁለት ሰዎች ተደግፎ ሲራመድ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ፍንዳታው የተፈጠረው በፖሊስ ዋና መሥሪያ ቤት አቅራቢያ በሚገኝ መስጊድ ላይ ነው

    በፓኪስታን ቦምብ የተጠመደበት ተሽከርካሪ ከመስጊድ ጋር ተጋጭቶ አምስት የፖሊስ መኮንኖችን ጨምሮ ቢያንስ 16 ሰዎች መሞታቸውን አንድ ከፍተኛ የፖሊስ መኮንን አስታወቁ።

    በካይበር ፓክቱንክዋ ግዛት ኮሃት ከተማ የፖሊስ ዋና መሥሪያ ቤት አቅራቢያ በሚገኘው መስጊድ በጥቃት ፈፃሚዎቹ እና በጸጥታ ኃይሎች መካከል እየተደረገ ያለው የተኩስ ልውውጥ መቀጠሉም ተገልጿል።

    ከጥቃት አድራሾቹ አንደኛው መገደሉ የተገለጸ ሲሆን የፖሊስ ባለሥልጣኑ የነፍስ አድን ጥረት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

    ጥቃቱን ተከትሎ የአገሪቷ ፕሬዚደንት አሲፍ አሊ ዛርዳሪ በሰጡት መግለጫ፣ በፍንዳታው ጉዳት የደረሰባቸው ግለሰቦች በፍጥነት እንዲያገግሙ መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ሙሃማድ ሸህባዝ ሻሪፍም ጥቃቱን አውግዘዋል።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል እንደዘገበው የካይበር ፓክቱንክዋ ግዛት ፖሊስ ኃላፊ ኢንስፔክተር ጀነራል ኡልፊካር ሃሚድ ጥቃቱ "አጥፍቶ መጥፋት" እንደሆነ ገልጸዋል።

    ሆኖም ለጥቃቱ እስካሁን ኃላፊነቱን የወሰደ አካል የለም።

    ከቅርብ በራት ወዲህ ጦሩን እና ፖሊስን ዒላማ ያደረጉ የታጣቂዎች እንቅስቃሴ በአገሪቷ ድንበሮች አካባቢ በከፍተኛ ሁኔታ ጨምሯል።

    ኢስላማባድ ታጣቂዎች ለመሰልጠን እና በፓኪስታን ላይ ጥቃት ለመፈፀም አፍጋኒስታን እንደ ምቹ መደበቂያ ይጠቀማሉ ስትል ከስሳለች።

    የአፍጋኒስታን የታሊባን መንግሥት ግን ክሱን ያጣጣለ ሲሆን የታጣቂዎች እንቅስቃሴ የፓኪስታን የውስጥ ችግር ነው ብሏል።

  9. የኒጀር ወታደራዊ ባለሥልጣናት የቀድሞውን ጠቅላይ ሚኒስትር ጨምሮ የአምስት ሰዎችን ዜግነት ነጠቁ

    ጄነራል አብዱራህማን ቲቺያኒ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የምስሉ መግለጫ, የኒጀር ወታደራዊ መሪው ጄነራል አብዱራህማን ቲቺያኒ

    የኒጀር ወታደራዊ ባለሥልጣናት የአገሪቷን የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር እና ከቀድሞው አስተዳደር ጋር ግንኙነት ያላቸውን የአምስት ሰዎችን ዜግነት ነጠቁ።

    በወታደራዊ መሪው ጄነራል አብዱራህማን ቲቺያኒ የተፈረመው ትዕዛዝ የቀድሞውን ጠቅላይ ሚኒስትር ኡሆሞውዶ ማህመዱን እና ሌሎች ግለሰቦችን በስም ጠቅሷል።

    በመንግሥት የሚተዳደረው 'ኒጀሪያን ዲ ፕረስ' እንደዘገበው አምስቱ ግለሰቦች የሕግ ሥርዓትን የሚያናጋ ሐሰተኛ መረጃን በማሠራጨት፣ ከውጭ ኃይሎች ጋር በመተባበር፣ በስም ማጥፋት፣ የጦሩን እና የአገሪቷን ክብር የሚነኩ ድርጊቶች ላይ በመሳተፍ እንዲሁም ብሔራዊ ጦሩን እና ማኅበራዊ ግንኙነቱን በማጣጣል ተከስሰዋል።

    እነዚህ ክሶች የቀረቡባቸው አብዛኞቹ ግለሰቦች ሐምሌ 2023 ሥልጣን የተቆጣጠሩትን ወታዳራዊ ባለሥልጣናት ከሚቃወመው የቀድሞው አስተዳደር ጋር ግንኙነት ያላቸው ናቸው።

    ዜግነታቸው ከተነጠቁት አንዱ የሆኑት ኦሆሞዶ ማህማዶ በመፈንቅለ መንግሥት በተገረሰሱት ፕሬዝዳንት ባዞም የሥልጣን ዘመን ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው አገልግለዋል።

    የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ አምስቱ ግለሰቦች ከኒጀር ውጭ እንደሚኖሩ የሚታመን ሲሆን፣ የት እንዳሉ ግን ትዕዛዙ የተላለፈበት ደብዳቤ አልጠቀሰም።

    ቢቢሲ የተወሰኑትን ግለሰቦች ለማነገጋር ጥረት ቢያደርግም በተወሰደው እርምጃ ላይ አስተያየት አልሰጡም።

    ወታደራዊ ባለሥልጣናቱ አሁን ላይ የወሰዱት እርምጃ በ2024 ወታደራዊው አስተዳደር ከተቋቋመ በኋላ ዜግነታቸውን የተነጠቁ ኒጀራዊያንን ቁጥር 25 አድርሶታል።

    ቀደም ብሎ በተወሰዱት እርምጃዎች የቀድሞ ሚኒስትሮች፣ የፖለቲካ አክቲቪስቶች እና ከቀድሞው ፕሬዝዳንት ባዙም አስተዳደር ጋር ግንኙነት ያላቸው ሰዎች ዒላማ ተደርገዋል።

    የሰብዓዊ መብት ተሟጋቹ ሂውማን ራይትስ ዎች እርምጃው አገር አልባ የመሆንን አደጋ የሚያባብስ እንደሆነ ገልጾ፣ ከ2024 መጨረሻ አንስቶ ቢያንስ 18 በውጭ የሚኖሩ ተቃዋሚዎች በጊዜያዊነት ዜግነታቸውን መነጠቃቸውን ጠቅሷል።

    ወታደራዊ አስተዳደሩ ግን እርምጃው ብሔራዊ ደኅንነትን ለመጠበቅ እና ሕግ ለማስከበር የተወሰደ ነው በማለት ራሱን ተከላክሏል።

    ሆኖም የመብት ተሟጋች ቡድኖች ወታደራዊ አስተዳደሩ ትችት በሚሰነዝሩበት ላይ እየወሰደ ያለውን እና እየጨመረ የመጣውን የዜግነት ነጠቃ እርምጃ በጥብቅ ተችተዋል።

  10. በናይጄሪያ እስር ቤት ውስጥ በሕገ ወጥ ማዕድን ማውጣት ተጠርጥረው የታሰሩ በርካታ ሰዎች ሞቱ

    የታጠቀ የናይጄሪያ የደኅንነት እና የሲቪል መከላከያ ጓድ አባል

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    በሰሜን ማዕከላዊ ናይጄሪያ በሕገ ወጥ ማዕድን ማውጣት ተጠርጥረው የታሰሩ 37 ሰዎች በእስር ቤት ውስጥ መሞታቸውን የአካባቢ ባለሥልጣናት ገለጹ።

    የእስረኞቹ ሞት መንስኤ ምን እንደሆነ ለማጣራት ፖሊስ ምርመራ የጀመረ ሲሆን፣ የናይጄሪያ የደኅንነት እና የሲቪል መከላከያ ጓድ ሞቶቹ የተከሰቱት በበሽታ ወረርሽኝ ሳቢያ እንደሆነ ገልጿል።

    ይሁን እንጂ፣ ለፈረንሳዩ የዜና ወኪል ኤኤፍፒ የደረሰ የደኅንነት መረጃ፣ እስረኞቹ የሞቱት በማረሚያ ቤቱ ውስጥ በነበረው ከፍተኛ መጨናነቅ እና የአየር ዝውውር ማነስ ምክንያት መሆኑን ያመለክታል።

    ማረሚያ ቤቱ የሚገኘው በናይጄሪያ ኒጀር ግዛት ውስጥ ነው።

    የግዛቱ አስተዳዳሪ ሞሐመድ ኡማሩ ባጎ ሐሙስ ዕለት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ በእረኞቹ ላይ የደረሰውን ሞት “አሳዛኝና አስከፊ” ሲሉ ገልፀዋል።

    ከክስተቱ ጋር በተያያዘ አንድ የናይጄሪያ የደኅንነት እና የሲቪል መከላከያ ጓድ አዛዥ ታስሯል ሲሉም ባጎ አክለዋል።

    በተጨማሪም የሦስት ቀናት የሐዘን ጊዜ አውጀው፣ ለጥር ወር የታቀደው የምርጫ ዘመቻ እንዲዘገይ አድርገዋል።

    ባለሥልጣናት፣ በማዕድን ሀብት በበለጸገችው የኒጀር ግዛት በምትገኘው ቦርጉ አካባቢ በሕገ ወጥ የማዕድን ማውጣት ተግባር የተጠረጠሩ ወጣቶችን ማክሰኞ እለት ነበር በቁጥጥር ስር ያዋሉት። አካባቢው በአነስተኛ መጠን የወርቅ ማዕድን ማውጣት በስፋት የሚካሄድበት ቦታ ነው።

    የናይጄሪያ የደኅንነት እና የሲቪል መከላከያ ጓድ በሚያስተዳድረው እስር ቤት ውስጥ ከታሰሩት ተጠርጣሪዎች መካከል 37 ሰዎች ሞተው የተገኙት ከሁለት ቀናት በኋላ ነው።

  11. በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ ኢራናውያን መንግሥትን በመደገፍ አደባባይ ወጡ

    ሠልፈኞች

    የፎቶው ባለመብት, AP

    ላለፉት ሁለት ወራት ከአሜሪካ ጋር ጦርነት ውስጥ የቆየው የኢራን መንግሥት ባዘጋጀው ሠልፍ ላይ በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ ሠልፈኞች መታደማቸውን የፈረንሳዩ የዜና ወኪል ዘገበ።

    ሠልፈኞቹ አስፈላጊ ከሆነ ታጥቀው ከመንግሥት ጎን ለመቆም ዝግጁ መሆናቸውን ሲናገሩ ተደምጠዋል።

    የኢራን መንግሥት ሕዝቡን ለማስተባበር እና ብሔራዊ አንድነትን ለማጠናከር ጥረት እያደረገ ነው ተብሏል።

    ሠልፉ የተካሄደው የአሜሪካ የባህር ኃይል ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን ካገደ እንዲሁም በመንግሥት ላይ የምጣኔ ሃብት ጫና ለመጨመር በሚል አሜሪካ አዳዲስ ማዕቀቦች ከጣለች በኋላ ነው።

    “ሕይወታቸውን ለኢራን መስዋዕት ለማድረግ ዝግጁ የሆኑ” በሚል በጎ ፈቃደኞች ወታደራዊ ሥልጠና እየወሰዱ ሲሆን እስካሁን ምን ያህል ሰዎች እንደሠለጠኑ በይፋ አይታወቅም።

    በቴህራን የተካሄደው ሠልፍ ላይ የታደሙ ሰዎች ወታደራዊ አልባሳትን ለብሰው፣ ባንዲራ ይዘው መፈክር ሲያሰሙ ታይተዋል።

    ለቀናት የአገሪቱ ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን ሰልፉን ለመታደም የአገሪቱ ዜጎች አደባባይ እንዲወጡ ሲቀሰቅሱ ነበር።

    መገናኛ ብዙኃኑ በቅርቡ በጎ ፈቃደኞች ከመሳሪያ ጋር ስልጠና እንደሚሰጣቸው የዘገቡ ሲሆን በጎ ፈቃደኞቹ የአብዮታዊ ዘቡ አጋር እንደሚሆኑ ተናግረዋል።

    የቴህራን ዘብ አዛዥ የሆኑት ጄነራል ሃሳን ሃሳንዛዴህ ለአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን 600,000 ሰዎች በበጎ ፈቃድ ወታደራዊ ሥልጠና ለመውሰድ መመዝገባቸውን ተናግረዋል።

    አንድ ሚሊዮን ሰዎች በሥልጠናው ላይ ይሳተፋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅም ጨምረው ተናግረዋል።

    አርብ ማለዳ መገናኛ ብዙኃኑ 300,000 ያህል ሰዎች አደባባይ መውጣታቸውን ዘግበዋል።

    አዲሱ የባሲጅ አዛዥ ሆሴን ታኤብ፣ በጎ ፈቃደኞቹ “ለተሟላ መከላከያ” ዝግጁ እንደሚደረጉ ገልፀው በሌሎች ከተሞችም ተመሳሳይ ሠልፍ እንደሚካሄድ ተናግረዋል።

    አዲሶቹ ሠልጣኞች ለኢራን ጠላቶች “ቅዠት” እንደሚሆኑባቸው ታኢብ ተናግረዋል።

    በቴህራን የተደረገው ሕዝባዊ ሠልፍ ላይ ፕሬዚዳንት ማሱድ ፔዙሽኪያን፣ ወታደራዊ አዛዦች እና ከፍተኛ ባለሥልጣናት ተገኝተዋል።

    አንዳንድ ሠልፈኞች የአሜሪካ እና እስራኤልን ባንዲራዎችን ሲረጋግጡ ታይተዋል። ሌሎች ደግሞ “ሞት ለአሜሪካ” እንዲሁም "ሞት ለእስራኤል" የሚሉ መፈክሮችን አሰምተዋል።

    ከትንሽ ልጇ እና ከባለቤቷ ጋር በሰልፉ ላይ የተገኘችው የ24 ዓመቷ ማርዚህ አፋጊ “እዚህ የተገኘሁት ትራምፕ፣ በእኛ በኢራናውያንና በአገራችን ላይ ለሚሰነዝሩት ማስፈራሪያ ምንም ዓይነት ፍርሃት እንደሌለን ልነግራቸው ነው” ብላለች። “በታሪክ ውስጥ ማንም ሰው ኢራንን ወርሮ እዚህ መቆየት አልቻለም።”

    በሠልፉ ላይ ሚሳዔሎች እና ድሮኖች ለእይታ ቀርበዋል።

    የኢራን ባንዲራ የያዘ ሰው

    የፎቶው ባለመብት, AP

  12. ጂቡቲ በሁቲ ታጣቂዎች ላይ ለሚካሄድ ወታደራዊ ዘመቻ ግዛቷን እንደማትፈቅድ አስታወቀች

    የጂቡቲ ፋይናንስ ሚኒስትር ኢሊያስ ሙሳ ዳዋሌ

    የፎቶው ባለመብት, SM

    የምስሉ መግለጫ, የጂቡቲ ፋይናንስ ሚኒስትር ኢሊያስ ሙሳ ዳዋሌ

    የጂቡቲ የገንዘብ ሚኒስትር ኢሊያስ ሙሳ ዳዋሌ አገራቸው በሁቲ ታጣቂዎች ላይ ለሚካሄድ ማንኛውም ወታደራዊ ዘመቻ ግዛቷን እንደማትፈቅድ አስታወቁ።

    ሚኒስትሩ ከቢቢሲ ሶማልኛ ጋር በነበራቸው ቆይታ ከዚህ ቀደም አሜሪካ በአገሪቱ ያላትን ጦር ሠፈር በሁቲ ላይ ዘመቻ ለማካሄድ እንድትጠቀም አለመፍቀዷን አስታውሰው አhuንም የተለወጠ አቋም አለመኖሩን አስረድተዋል።

    ጂቡቲ በየትኛውም ወታደራዊ ዘመቻ ውስጥ መሳተፍ እንደማትፈልግ የተናገሩት ሚኒስትሩ፣ በየመን በተለያዩ ወገኖች መካከል እየተካሄደ ያለው ግጭት በሰላማዊ መንገድ መፈታት እንዳለበት ተናግረዋል።

    ጂቡቲ ለቀጣናው ኃያላን ጦር ማሰባሰቢያ ማዕከል አትሆንም ያሉት የገንዘብ ሚኒስትሩ ዳዋሌ፣ አገሪቱ የራሷ ከፍተኛ ኃላፊነቶችና ጫናዎች እንዳሉባት ገልጸዋል።

    ጂቡቲ በኤደን ባሕረ ሰላጤ አቅራቢያ የምትገኝ ስትሆን ለየመን እና ባብ ኤል ማንዳብ ወሽመጥ በቅርብ ርቀት ላይ ትገኛለች።

    ሚኒስትሩ የባብ ኤል ማንዳብ ወሽመጥን ክፍት አድርጎ መቆየት ለጂቡቱ ቁልፍ ጉዳይ መሆኑን ከቢቢሲ ጋር በነበራቸው ቆይታ ወቅት አስረድተዋል።

    ጂቢቱ በየመን እየተዋጉ የሚገኙ አካላት ሰላማዊ መፍትሄ እንዲፈልጉ ጠይቀው አገራቸው ባሕር ተሻግሮን የሚመጣ አለመረጋጋት እንደማትፈልግ ተናግረዋል።

    በየመን እየተባባሰ የመጣው ግጭት በጂቡቲ ላይ የሰብዓዊ ጫና እያሳደረ መሆኑን ያስረዱት የገንዘብ ሚኒስትሩ፣ በርካቶች ተፈናቅለው ወደ አገራቸው መግባታቸውን አስረድተዋል።

    በግጭቱ ምክንያት ቤት ንብረታቸውን ጥለው ለመሰደድ የተገደዱ በርካታ ሴቶች እና ሕጻናት ወደ ጂቡቲ መድረሳቸውን ጨምረው አስታውቀዋል።

    ከየመን የሚነሱ አነስተኛ ጀልባዎች ጂቡቲ ለመድረስ ከአንድ ሰዓት ያነሰ ጊዜ ብቻ የሚፈጅባቸው ሲሆን ይህም በርካቶች ወደ አገሪቱ እንዲሸሹ አድርጓቸዋል ሲሉ አብራርተዋል።

    የጂቡቲ መንግሥት ዋነኛ ኃላፊነት የአገሪቱን ሕዝቦች ሰላም እና ደህንነት መጠበቅ ነው ያሉት የገንዘብ ሚኒስትሩ፣ በየመን ውስጥ የተከሰተው ማንኛውም አለመረጋጋት በአገራቸው ውስጥ ለሚኖረው ተጽዕኖ መንግሥታቸው ዝግጁ መሆኑን ተናግረዋል።

    የዓለም አቀፍ መንግሥታት ለተፈናቃዮቸ ተገቢውን ድጋፍ እንዲያደርጉ የጠየቁት ሚኒስትሩ ግጭትን ሸሽተው ጂቡቲ የገቡት ዜጎች "ያለ በቂ ድጋፍ መተው የለባቸውም" ብለዋል።

    ዳዋሌ የጂቡቲ ጎረቤቶቿች በተለይ ደግሞ በባሕረ ሰላጤው የሚገኙ አገራት ለየመን ግጭት መፍትሄ ለመስጠት እንዲሰሩ ጥሪ አቅርበዋል።

    ሚኒስትሩ ጂቡቲ የባብ ኤል ማንዳብ የባሕር መስመር ክፍት ሆኖ እንዲቀጥል ድጋፏን እንደምትሰጥ የገለጹ ሲሆን፣ በግጭቱ ውስጥ የተሳተፉ ወገኖችም መረጋጋትን በመላበስ ሰላማዊ መፍትሄ እንዲፈልጉ ጥሪ አቅርበዋል።

  13. በለንደን ለሰባት ዓመታት ጠፍታ የነበረች ሴት አስከሬን በሰደድ እሳት በተቃጠለ ቁጥቋጦ ውስጥ ተገኘ

    የሦስት ልጆች እናት እና የ44 ዓመት ጎልማሳ የሆነቸው ጆአን ሼን

    የፎቶው ባለመብት, Police handout

    በደቡብ ምዕራብ ለንደን የተከሰተን ሰደድ እሳት ተከትሎ ለሰባት ዓመት ያህል ስትፈለግ የነበረች ሴት አስከሬን ተገኘ።

    የሦስት ልጆች እናት እና የ44 ዓመት ጎልማሳ የሆነቸው ጆአን ሼን የጠፋችው እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2019 ኅዳር ወር ላይ ነው።

    የሜትሮፖሊታን ፖሊስ አባላት እአአ ነሐሴ 12 በእሳት በወደመው ቁጥቋጦ ውስጥ የሰው አጽም መገኘቱን ተከትሎ ወደ ስፍራው ተጠርተዋል።

    ፖሊስ ግለሰቧን በመግደል የጠረጠረውን የ56 ዓመት ጎልማሳ በቁጥጥር ስር አውሏል።

    በለንደን የሚገኙ መርማሪዎች የተገኘው አጽም የሼን መሆኑን ካረጋገጡ በኋላ ምርመራውን ለአካባቢው ፖሊስ አሳልፈው ሰጥተዋል።

    ሼን በጠፋችበት ወቅት ፖሊስ ሰፊ እና ውስብስብ ምርመራ ማድረጉን የገለጸ ሲሆን ከ4,000 በላይ ፍንጮችን በመከተል ከ300 በላይ ቃሎችን ተቀብያለሁ ብሏል።

    ከዚህም በተጨማሪ ከ10 በላይ አድራሻዎች እና በርካታ ተሽከርካሪዎች ላይ ዝርዝር ፍተሻ አካሂዷል።

    ፖሊስ የሼን አስከሬን መገኘቱን ተከትሎ አሁንም ስለ አጠፋፏ መረጃ ያለው ማንኛውም ሰው እንዲተባበረው ጠይቋል።

    ነሐሴ 5 ከሁለት ሄክታር በላይ ያወደመ እሳት በተቀሰቀሰበት ወቅት የለንደን የእሳት አደጋ ሠራተኞች ተጠርተው እሳቱን ያጠፉ ሲሆን ከሳምንት በኋላ አጽሙ ተገኝቷል።

    አጽሙ ላይ ምርመራ ከተደረገ በኋላ ሟች እድሜዋ ከ25 እስከ 45 መካከል የሆነ ሴት እንደሆነች ይፋ ተደርጓል።

    የሜትሮፖሊታን ፖሊስ ቃል አቀባይ አጽሙ የተገኘው በአካባቢው ነዋሪ መሆኑን ይፋ አድርገዋል።

    ምርመራውን ለሚተባበር ማንኛውም ግለሰብ 20,000 ፓውንድ ሽልማት ማዘጋጀቱንም ፖሊስ ጨምሮ ገልጿል።

    የሼን ቤተሰቦች መጥፋቷን ለፖሊስ ያስመዘገቡት እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2020 የካቲት ወር ነው።

    በ2020 በርካታ ሰዎች በነፍስ ማጥፋት ወንጀል ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር ውለው ነበር።

    ፖሊስ ግለሰቧ ቋሚ የመኖሪያ አድራሻ፣ መኪና ወይንም የባንክ አካውንት እንደሌላት አስታውቆ ነበር።

  14. የፋኖ እንቅስቃሴ “በአማራ ክልል ብቻ የተወሰነ አይደለም” ያለው አፋብን በአበሽጌው ጥቃት ላይ ተሳትፎ እንደሌለው ገለፀ

    የአማራ ታጣቂዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በጉራጌ ዞን አበሽጌ ወረዳ ጥቃት የፈፀሙ ታጣቂዎች የአፋብን አባላት እንዳልሆኑ የድርጅቱ ቃል አቀባይ አስረስ ማረ ዳምጤ ለቢቢሲ ተናገሩ።

    በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጉራጌ ዞን አበሽጌ ወረዳ ውስጥ ሰኞ መስከረም 4/2018 ዓ.ም. በተፈፀመ ጥቃት በርካታ ሰላማዊ ሰዎች መገደላቸውን እና መታገታቸውን የአካባቢው ነዋሪዎች እና የክልሉ ሰላም እና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ ለቢቢሲ ገልፀዋል።

    ካነጋገርናቸው መካከል አንዱ፣ 15 ሰዎች የጥቃቱ ሰለባ መሆናቸውን እንዳረጋገጡም አስረድተዋል።

    ከተገደሉት በተጨማሪ እስከ 20 የሚደርሱ ሰዎች በታጣቂዎች መታገታቸውንም የገለፁት ነዋሪዎቹ፣ ጥቃቱ የተፈፀመባት ዋልጋ ተብላ የምትጠራ አነስተኛ ከተማ ነዋሪዎች ቀያቸውን ለቀው መፈናቀላቸውንም አክለው ገልፀዋል።

    የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሰላም እና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ አቶ ተመስገን ካሳ በበኩላቸው፣ በጥቃቱ ስለደረሰው ጉዳት የሚያጣራ ቡድን ተቋቁሞ ወደ ስፍራው መላኩን እና ሥራውን አጠናቆ ሪፖርት ገና አለማቅረቡን ገልፀዋል።

    ጥቃት ፈፃሚዎቹ ራሳቸውን “ፋኖ” ብለው የሚጠሩ ታጣቂዎች መሆናቸውን ያነጋገርናቸው ነዋሪዎች እና የክልሉ ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊው ገልፀዋል።

    የአማራ ፋኖ ብሔራዊ ንቅናቄ (አፋብን) በበኩሉ በአበሽጌው ጥቃት ላይ ተሳትፎ የለኝም ብሏል።

    የአፋብን ቃል አቀባይ አስረስ ማረ ዳምጤ፣ የድርጅቱ እንቅስቃሴ "በአማራ ክልል ብቻ የተወሰነ እንዳልሆነ" ገልፀው፣ "አበሽጌ ወረዳ በንፁሃን ላይ ተፈፀመ የተባለውን ጥቃት በተመለከተ ግን እንደ አማራ ፋኖ ብሔራዊ ንቅናቄ ኃላፊነት አንወስድም" ሲሉ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    በአበሽጌም ይሁን በሌላ አካባቢ "ራሳቸውን ለመከላከል የሚደራጁ በፋኖነት ራሳቸውን የሚጠሩ ወጣቶች እንዳሉ እናምናለን" ሲሉም አክለዋል።

    ለአብነትም “ወለጋ አካባቢ የሚንቀሳቀሰው በድርጅታችን ‘ቼይን ኦፍ ኮማንድ’ [የዕዝ ሰንሰለት] ስር ያለ፣ ነገር ግን ንፁሃንን ለማጥቃት ሳይሆን ከመከላከያ ሠራዊቱ፣ ገዳ ኮማንዶ ከሚባለው ጨፍጫፊ ኃይል እና በተለያየ ስም እና መልክ ከተደራጀ የአገዛዙ ኃይል ጋር የሚታገል ንፁሃንን የሚጠብቅ የራሱ ‘ቼይን ኦፍ ኮማንድ’ እና አመራር ያለው ከድርጅታችንም ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ያለው ነው” ብለዋል።

    ይሁን እንጂ፣ የአበሽጌውን "ጥቃት ፈፀሙት ተብሎ ክስ እየቀረበባቸው ያሉ ሰዎች በድርጅታችን 'ቼይን ኦፍ ኮማንድ' [የዕዝ ሰንሰለት] ስር የምናውቃቸው አይደሉም" በማለት አፋብን እውቅና የሰጠው ታጣቂ ቡድን በስፍራው አለመኖሩን አስረድተዋል።

  15. አሜሪካ የኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣናት በመንግሥታቱ ድርጅት ጉባዔ ላይ እንዲሳተፉ ቪዛ ሰጠች

    ማርኮ ሩቢዮ

    የፎቶው ባለመብት, AP

    የትራምፕ አስተዳደር በሚቀጥለው ሳምንት በመንግሥታቱ ድርጅት ጉባዔ ላይ ለመሳተፍ ወደ ኒውዮርክ ለሚያመሩ የኢራን ልዑካን ቪዛ ሰጠ።

    ሁለቱ አገራት ጦርነት ውስጥ ቢሆኑም አሜሪካ የኢራን ፕሬዚዳንት እና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትርን ጨምሮ ለልዑካን ቡድኑ አባላት ቪዛ መስጠቷን አስታውቃለች።

    የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሐሙስ ዕለት ለኢራን “ወሳኝ ልዑካን” ከአስፈላጊ ባልደረቦቻቸው ጋር በመንግሥታቱ ድርጅት ጉባዔ ላይ መሳተፍ እንዲችሉ ቪዛ መስጠቱን አስታውቋል።

    ለፈረንሳዩ የዜና ወኪል ስማቸው እንዳይገለጽ በመጠየቅ አስተያየታቸውን የሰጡ አንድ ባለሥልጣን ወሳኝ ልዑካን የተባሉት ፕሬዚዳንቱ ማሱድ ፔዜሽኪያን እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አባስ አራግቺ መሆናቸውን ተናግረዋል።

    አሜሪካ ከስድስት ወር በላይ ከኢራን ጋር ጦርነት ውስጥ እያለች ይህንን እርምጃ መውሰዷ ያልተለመደ መሆኑ ተገልጿል።

    አሜሪካ እና ኢራን ወደ ድርድር ጠረጴዛ የመመለስም ሆነ የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግም የመክፈት ምንም ምልክት አላሳዩም።

    በየመን የሚገኙት የሁቲ ታጣቂዎችም በሳዑዲ የነዳጅ መሠረተ ልማቶች እና መርከቦች ላይ የሚፈጽሙትን ጥቃት ማቆማቸው ተነግሯል።

    በተጨማሪም፣ አሜሪካ ቴህራን በዓለም ላይ ሽብርተኝነትን በይፋ የምትደግፍ ዋነኛ ሀገር ሆና ቀጥላለች በማለት ከፍተኛ ማዕቀቦችን ጥላለች።

    አሜሪካ በቅርብ ሳምንታት ውስጥ የቴህራንን "ወሳኝ የሆኑ የገንዘብ አቅርቦት መስመሮችን" ለማቋረጥ ያለመ አዲስ ዘመቻ ጀምራለች።

  16. ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ አቅራቢያ የአሜሪካን ድሮን መትታ መጣሏን አስታወቀች

    ኤምኪው -9 የተሰኘ የአሜሪካ ድሮን

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ ሐሙስ ዕለት ኤምኪው -9 የተሰኘ የአሜሪካ ድሮን በሆርሙዝ ወሽመጥ አቅራቢያ መትቶ መጣሉን አስታወቀ።

    አብዮታዊ ዘቡ ባወጣው መግለጫ ሰው አልባ አውሮፕላኑን መትቶ የጣለው በቄሸም ደሴት መሆኑን ገልጿል።

    አክሎም በኢራን ጦር ኃይሎች ተመትቶ የወደቀ 53ኛ ኤምኪው-9 ድሮን መሆኑን ጠቅሷል። የአሜሪካ ጦር ተመትቶ ወድቋል ስለተባለው ሰው አልባ አውሮፕላን እስካሁን ድረስ ያለው ነገር የለም።

    አብዮታዊ ዘቡ ድሮኑ ተመትቶ የወደቀው ሐሙስ ዕለት ማለዳ መሆኑን ገልጾ፣ በተሻሻለ የአየር መከላከያ ስርዓት በመጠቀም መለየቱን እና ማውደሙን አስታውቋል።

    ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ አካባቢ የሚደረጉ የድሮን በረራዎችን እንደምትጠልፍ እና እንደምትመታ አስታውቃለች።

    የካቲት 21 2018 ዓ.ም. አሜሪካ እና እስራኤል በጋራ በመሆን ቴህራን ላይ ጦርነት ከከፈቱ ወዲህ ኢራን የአጸፋ እርምጃ በመውሰድ በባህረ ሰላጤው አገራት ላይ ጥቃት ፈጽማለች።

    ይህ በእንዲህ አንዳለ የእስላማዊ ሪፐብሊኩ መሪ የፖለቲካ አማካሪ የሆኑት ሞሐመድ ባቃር ዞልቃድር ኢራን የአሜሪካው ፕሬዚዳንት እና የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር “ከሥልጣን እስኪወርዱ ድረስ” የሆርሙዝ ወሽመጥን እንደማትከፍት ተናግረዋል።

    አማካሪው የጦርነቱ የተጀመረበት 200ኛ ቀንን በማስመልከት በሰጡት ቃለ ምልልስ አገራቸው አሜሪካን እና እስራኤልን መገዳደሯን እንደምትቀጥል እና የሆርሙዝ ወሽመጥ መዘጋት “የኢራን ሕዝብ የመጀመርያ ደረጃ የበቀል እርምጃ” መሆኑን ተናግረዋል።

    ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ያለው ውጥረት በሆርሙዝ ወሽመጥ መከፈት ላይ ያተኮረ ሆኗል።

  17. የደቡብ አፍሪካ ፖሊስ በጆሃንስበርግ ተገድላ የተጣለች ዘጠነኛዋን ሴት አስከሬን ማግኘቱን አስታወቀ

    አስከሬኑ የተገኘው በጆነሃንስበርግ በዳውን ፓርክ የመንገድ ዳርቻ ላይ በጨርቅ ተጠቅልሎ ነው

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የሟቿ አስከሬን የተገኘው በጆነሃንስበርግ በዳውን ፓርክ የመንገድ ዳርቻ ላይ በጨርቅ ተጠቅልሎ ነው

    የደቡብ አፍሪካ ፖሊስ በጆሃንስበርግ ከተማ በተከታታይ የተገደሉ ሴቶችን ጉዳይ እየመረመረ ባለበት ወቅት የዘጠነኛዋን ሴት አስከሬን ማግኘቱን አስታወቀ።

    የዘጠኙ ሴቶች ገዳዮች ያልተያዙ ሲሆን በጆሃንስበርግ ነዋሪዎች ዘንድ ፍርሃትን እና ቁጣን ቀስቅሷል።

    ፖሊስ ሐሙስ ማለዳ አስከሬኗን ያገኛት ይህች ሴት በከፊል እርቃኗን የነበረች ሲሆን በከፊል በጨርቅ ተጠቅልላ ከመንገድ ዳር ተጥላ ነበር ተብሏል።

    የሟቿ ማንነት እስካሁን ድረስ አልታወቀም።

    ከሐምሌ ወር አጋማሽ ጀምሮ በጆሃንስበርግ ከተማ ተገድለው የተጣሉ ሴቶች ቁጥር ስምንት ደርሶ ነበር።

    በርካታዎቹ ሴቶች በከፊል ተራቁተው፣ ጉዳት እንደደረሰባቸው ከሚያሳይ ግልጽ ምልክት ጋር የተገኙ ሲሆን ፖሊስ የሁሉም ሞት የተያያዘ ስለመሆኑ የሚያሳይ መረጃ እስካሁን አለማግኘቱን አስታውቋል።

    ፕሬዚዳንት ሲሪል ራማፎሳ የሴቶቹን ገዳይ በቁጥጥር ስር ለማዋል “የማንፈነቅለው ድንጋይ የለም” ሲሉ ተናግረዋል።

    ፖሊስ ግድያዎቹን አንድ ግለሰብ የፈጸማቸው ወንጀሎች ስለመሆናቸው ድምዳሜ ላይ ባይደርስም ቡድኖች ከወንጀሉ ጀርባ ሊኖሩ እንደሚችሉ ጥርጣሬ እንዳለው ገልጿል።

    የፖሊስ ቃል አቀባይ ብርጋዴር አትሌንዳ ማቴ "እነዚህ እዚህም እዚያም የሚፈጸሙ ተመሳሳይ ወንጀሎች ሊሆኑ ይችላሉ፤ ነገርግን እስካሁን ድረስ ግንኙነት እንዳላቸው የሚያሳይ ፍንጭ አላገኘንም" ብሏል።

    ከመጀመርያው አስከሬን ጋር በተያያዘ አንድ ግለሰብ ተጠርጥሮ በቁጥጥር ሥር የዋለ ሲሆን አሁንም በእስር ላይ እንደሚገኝ ተገልጿል።

  18. የመንግሥታቱ ድርጅት ባለሙያዎች አሜሪካ 'በኢራን የጦር ወንጀል ፈጽማለች ብሎ ለማመን የሚያስችል ምክንያት አለ' አሉ

    በአሜሪካ ጥቃት የወደመ አካባቢ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የመንግሥታቱ ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ባለሙያዎች ሐሙስ ዕለት አሜሪካ በኢራን ጦርነት የመጀመርያ ቀን በፈጸመቻቸው ሁለት ጥቃቶች የጦር ወንጀሎች ፈጽማለች ብሎ ለማመን የሚያስችል “አሳማኝ ምክንያት” መኖሩን ተናገሩ።

    የመንግሥታቱ ድርጅት የሰብዓዊ መብቶችን የሚመለከተው ቡድን የመደባቸው ባለሙያዎች አሜሪካ በፈጸማቻቸው እና ሴቶች እና ሕጻናትን ጨምሮ 178 ሰዎችን በገደሉት ሁለት ጥቃቶች ላይ ትኩረታቸውን አድርገው ምርመራ አድርገዋል።

    በተባበሩት መንግሥታት ድጋፍ የሚንቀሳቀሰው ቡድን "በግልጽ ሊለይ በሚችል" ትምህርት ቤት እና በደቡባዊቷ ላሜርድ ከተማ "በግልጽ ሊለይ በሚችል የስፖርት ማዕከል እና የመኖሪያ አካባቢ" ላይ በተፈጸሙት ሁለት የሚሳዔል ጥቃቶች የተነሳ የጦር ወንጀል ክሶችን አቅርቧል።

    የመንግሥታቱ ድርጅት እውነት አፈላላጊ ቡድን የኢራን ባለሥልጣናት የጸረ መንግሥት ሠልፎች ላይ በወሰዱት እርምጃ ሰብዓዊነት ላይ ወንጀሎች ፈጽመዋል ሲልም ተናግሯል።

    በጄኔቫ ለሚገኘው የተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት የሚቀርበው ይህ አዲስ ሪፖርት፤ በየካቲት ወር በተጀመረው የኢራን ጦርነት ወቅት የአሜሪካን ጥቃት እንዲሁም በታህሳስ ወር መጨረሻ በተቀሰቀሰው አገር አቀፍ ሁከት ላይ የኢራን መንግሥት የወሰደውን እርምጃ መርምሯል።

    ሮይተርስ በጄኔቫ ለሚገኙት የኢራን እና የአሜሪካ ቋሚ ተወካዮች ጥያቄ ቢያቀርቡም ወዲያውኑ ምላሽ አልሰጡም።

    የአሜሪካ ባለሥልጣናት ቀደም ሲል እንደገለጹት ወታደራዊ እንቅስቃሴዎች የሚከናወኑት በግጭት ወቅት ተግባራዊ የሚሆኑ ሕጎችን መሠረት በማድረግ መሆኑን የገለጹ ሲሆን በሌላ በኩል ኢራን ስልታዊ የመብት ጥሰት ፈጽማለች የሚሉ ክሶችን በተደጋጋሚ ውድቅ ስታደርግ ቆይታለች።

    የተባበሩት መንግሥታት ባለሙያዎች እንደገለጹት፣ በሚናብ በሚገኘው ሻጃሬህ ታይዬቤህ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ላይ ለተፈጸመውና ከ120 የሚበልጡ ተማሪዎችን ጨምሮ ከ150 በላይ ሰዎች ለሞቱበት ጥቃት የአሜሪካ ኃይሎች ተጠያቂ እንደሆኑ ለማመን የሚያስችል በቂ ምክንያት አግኝተዋል።

    ይህ ጥቃት በሰላማዊ ሰዎች ላይ ሞትና በሲቪል መሠረተ ልማቶች ላይ ጉዳት ያስከተለ፣ እንዲሁም በዓለም አቀፍ ሕግ መሠረት የጦር ወንጀል የሚያስቆጥር ጥቃት እንደነበር ባለሙያዎቹ ተናግረዋል።

  19. አሜሪካ ለሁለተኛ ጊዜ የፍልስጤም መሪ በተመድ ጉባዔ እንዳይሳተፉ አገደች

    ፕሬዝዳንት መሐሙድ አባስ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አሜሪካ ለፍልስጤም ፕሬዝዳንት መሐሙድ አባስ ቪዛ በመከልከል በተባበሩት መንግሥታት ጠቅላላ ጉባዔ እንዳይታደሙ ማገዷን ሁለት የፍልስጤም ምንጮች ለቢቢሲ ገለጹ።

    አሜሪካ አባስን በስም ሳትጠቅስ የቪዛ ክልከላውን ማራዘሟን አስታውቃለች። የቪዛ ክልከላው የተራዘመው ከሰላም ኮሚቴው የሚጠበቅባቸውን ባለመወጣታቸው ነው ተብሏል።

    ማዕቀቡ ለመጀመሪያ ጊዜ የተጣለው ባለፈው ዓመት ነሐሴ ላይ ነበር።

    አምና 80 ፍልስጤማውያን ባለሥልጣናት ቪዛ በመከልከላቸው በኒው ዮርክ የሚካሄደው ዓመታዊ የተመድ ጉባዔ ላይ መታደም አልቻሉም።

    አሜሪካ ባወጣችው መግለጫ የፍልስጤም አስተዳደር እና የፍልስጤም ነጻነት ድርጅት “ሽብርን ያወድሳሉ” ስትል ከስሳለች። የእስራኤል እና ፍልስጤም ግጭትን “ዓለም አቀፋዊ” ለማድረግ ሞክረዋል በማለትም ወንጅላለች።

    የፍልስጤም ባለሥልጣናት ለአሜሪካ ክስ እስካሁን ምላሽ አልሰጡም።

    ሆኖም ግን ከዚህ ቀደም ከትራምፕ አስተዳደር እና ከእስራኤል የቀረቡባቸውን ክሶች በተደጋጋሚ አስተባብለዋል።

    በዓለም አቀፍ ሕግ ሥር ወራሪ ኃይል ተጠያቂ እንዲደረግ የመጠየቅ መብት እንዳላቸውም ገልጸዋል።

    አምና አሜሪካ የቪዛ ክልከላ መጣሏን ተከትሎ የአባስ ተወካይ “ይሄ ግልጽ የዓለም አቀፍ ሕግ እና የተመድ ስምምነት ጥሰት ነው” ብለዋል።

  20. በኢራን እና ሩሲያ ላይ ማዕቀብ እንዲጣል የቀረበውን ረቂቅ የአሜሪካ ምክር ቤት አጸደቀ

    የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

    የአሜሪካ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በኢራን እና ሩሲያ ላይ ማዕቀብ እንዲጣል የቀረበውን ረቂቅ 262 ለ159 በሆነ ድምጽ አጸደቀ።

    ከምክር ቤቱ አስቀድሞ ሴኔት ያጸደቀው ረቂቅ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እንዲፈርሙበት የሚቀርብ ይሆናል።

    በረቂቁ ከቀረቡ ዕቅዶች መካከል የሩሲያ ባለሥልጣናት፣ የፋይናንስ ተቋማት፣ ባንኮች እንዲሁም የኢነርጂ እና መከላከያ ዘርፍ ላይ የሚጣለው ማዕቀብ ይጠቀሳል።

    ሩሲያ የተጣለባትን የነዳጅ ማዕቀብ በማለፍ ነዳጅ የምታዘዋውርባቸው መርከቦች (ሻዶ ፍሊት) ላይ ያነጣጠሩ ማዕቀቦችም ይገኙበታል።

    በረቂቁ መሠረት ትራምፕ ከሩሲያ ነዳጅ እና ጋዝ የሚገዙ አገራት ላይ 100% ታሪፍ መጣል ይችላሉ።

    ከሩሲያ ጋር ትስስር ያላት ኢራን ላይ የተጣሉ ማዕቀቦችን ማስፋፋትም የረቂቁ አካል ነው።

    ረቂቁ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከመላኩ በፊት በሴኔት 86 ለ11 በሆነ ድምጽ ጸድቋል።

    በአውሮፓውያኑ 1996 ኢራን ላይ የተጣለውን ማዕቀብ ከ2026 እስከ 2031 የሚያራዝም ነው።

    ረቂቁ አሁን ያለውን ማዕቀብ ሕጋዊ ትግበራ የሚያስጠብቅ ሲሆን፤ ተጨማሪ ግለሰቦች እና ተቋማት በማዕቀቡ ውስጥ አልተካተቱም።

    ሆኖም ግን ከሩሲያ ጋር ወታደራዊ ትብብር ያላቸው ተቋማት ላይ ማዕቀብ ይጥላል።