በግብጽ የደረሰ የድሮን ጥቃት በሲዊዝ ካናል የሚደረግ የመርከቦች እንቅስቃሴ ላይ ስጋት ፈጠረ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
በግብፅ የሜዲትራኒያን ባህር ዳርቻ በሚገኘው የዳሚዬታ ወደብ ላይ በሚገኙ ሁለት የጋዝ ማጓጓዣ መርከቦች ላይ እሳት ያስነሳው የድሮን ጥቃት፣ በስዊዝ ካናል በኩል የሚደረገው የመርከብ እንቅስቃሴ ላይ አዲስ ስጋት ፈጠረ።
በአሜሪካ እና በኢራን መካከል እየተባባሰ በመጣው ግጭት ወቅት የስዊዝ ካናል ለሳዑዲ ነዳጅ ንግድ ከቀሩት ዋና ዋና መስመሮች አንዱነው።
በዳሚዬታ ወደብ በሁለት መርከቦች ላይ እሳት እንዲነሳ ያደረገው የድሮን ጥቃት መሆኑን የግብፅ ካቢኔ ሐሙስ ዕለት አስታውቆ ነበር።
እስካሁን ድረስ ጥቃቱን በተመለከተ ኃላፊነት የወሰደ አካል የለም።
ወደቡ ሜዲትራኒያን እና ቀይ ባህርን የሚያገናኘው የስዊዝ ካናል አቅራቢያ ይገኛል።
የድሮን ጥቃት የአሜሪካ ንብረት በሆነው እና 'ኤነርጎስ ዊንተር' በተሰኘ የጋዝ ማከማቻ መርከብ ላይ ከደረሰ በኋላ እሳት የተነሳ ሲሆን ቃጠሎው ወደ ሌላ መርከብ መዛመቱን የዓይን እማኞች ለሮይተርስ ተናግረዋል።
ኢራን በዳሚዬታ በተፈጸመው ጥቃት ላይ ምንም ዓይነት ተሳትፎ እንደሌላት ገልጻለች።
"ግብፅ በቀጣናው ውስጥ አስፈላጊ ወዳጅና አጋር ስትሆን፣ ደህንነቷም ለእኛ እጅግ ወሳኝ ነው" ሲሉ የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ጽፈዋል።
"የቀጣናውን ሰላም ለማናጋት ታቅደው በሚከናወኑ የእስራኤል ሴራዎች እና የማጭበርበሪያ ድርጊቶች ላይ ሁላችንም ንቁ መሆን አለብን።"
አምስት ወር የሞላው የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚደረግ የመርከቦች እንቅስቃሴን በመግታት የዓለም ኤነርጂ አቅርቦት ላይ ከፍተኛ ጫና ፈጥሯል።
በኦማን እና በኢራን መካከል የሚገኘው ይህ መተላለፊያ ከግጭቱ በፊት የዓለም አንድ አምስተኛ ነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ ይጓጓዝበት ነበር።
በአሜሪካ እና በኢራን መካከል በሚካሄደው የሰላም ድርድር ወቅት ማነቆ ጉዳዮች መካከል አንዱ የወሽመጡ ጉዳይ ይገኝበታል።

























