ዩክሬን የሩሲያን ነዳጅ ማጣሪያ እና አየር ማረፊያ መምታቷን ስትገልጽ፤ ሞስኮ ስምንት ሰዎች መገደላቸውን አስታወቀች
ዩክሬን ወደ ሩሲያ ግዛት ዘልቃ በመግባት በፈጸመቻቸው ጥቃቶች የአገሪቱን ዋነኛ የነዳጅ ማጣሪያ እና የሩሲያ ስትራቴጂካዊ አቪዬሽን የሚገኝበትን አየር ማረፊያ መምታቷን ገልጻለች።
ከዩክሬን ድንበር 600 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኙት የኤንግልስ አየር ማረፊያ እና የነዳጅ ማጣሪያ መመታታቸውን የዩክሬን ፕሬዝዳንት ቭሎዲሚር ዜሌንስኪ ተናግረዋል።
እነዚህ መሠረተ ልማቶች የሩሲያን ጦርነት በገንዘብ ለመደገፍ እንደሚያገለግሉም ጠቅሰዋል። ፕሬዝዳንቱ ኤንግልስ አየር ማረፊያ እና ሳራቶቭ ነዳጅ ማጣሪያንም “ስትራቴጂካዊ ተቋማት” ሲሉ ገልጸዋቸዋል።
ካሉጋ ግዛት ውስጥ የሚገኝ የነዳጅ ዴፖ እና በብራያንስክ ያለ የድሮን ማስወንጨፊያ ስፍራም ጥቃት ተፈጽሞባቸዋል።
ሩሲያ በበኩሏ ዩክሬን በፈጸመቻቸው ጥቃቶች ስምንት ሰዎች መገደላቸውን እንዲሁም 635 ድሮኖችን መምታቷን እና መጥለፏን አስታውቃለች።
በተጨማሪም በሩሲያ ትልቁ የኦንላይን ችርቻሮ ንግድ ኩባንያ የሆነው ‘ዋይልድቤሪስ’ መጋዘን እንደተመታ ተገልጿል።
በሌላ በኩል ሞስኮ በጥቁር ባሕር የሚገኙ የዩክሬን ወደቦች እና ሁለት መርከቦች ላይ ጥቃት መፈጸሟን ተናግራለች።
ዩክሬንም በሰሜን ምሥራቅ ካርኪቭ ከተማ አቅራቢያ በሚገኝ የፖስታ ተርሚናል ላይ በተፈጸመው የሩሲያ ጥቃት አንድ ሰው መገደሉን ገልጻለች።
በሩሲያ እና ዩክሬን ጦርነት የሚገኙ ሠፊ የጦር ግንባሮች እንቅስቃሴ ሳይታይባቸው ባሉበት ቢሆኑም፣ ሁለቱም ወገኖች በዋና ዋና ከተሞች፣ በኤነርጂ መሠረተ ልማቶች እና መጋዘኖች ላይ የሚፈጽሟቸውን ጥቃት አጠናክረዋል።
ጦርነቱን ለመቋጨት በአሜሪካ የሚመራው የሽምግልና ሂደት እስካሁን ድረስ ውጤት አላመጣም።