ለዓለማችን የነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ አቅርቦት ወሳኝ የሆነው የሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ
የአሜሪካ የኢነርጂ መረጃ አስተዳደር (ኢአይኤ) በ2023 የመጀመሪያ አጋማሽ በቀን 20 ሚሊዮን በርሜል ነዳጅ እንዳለፈ ይገምታል።
ይህም በዓመት ወደ 600 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት የነዳጅ ንግድ በባሕር መስመሩ ላይ ይተላለፋል ማለት ነው።
በባሕር ወሽመጡ ላይ የሚከሰት ማንኛውም ዓይነት መስተጓጎል በዓለም አቀፍ ደረጃ የነዳጅ አቅርቦት ላይ ከፍተኛ መዘግየትን ሊያስከትል ይችላል፤ ይህም ወዲያውኑ በዓለም ዙሪያ የዋጋ ንረት እንዲፈጠር ያደርጋል።
ይህ ከባሕረ ሰላጤው አገራት በሚገባ የነዳጅ ዘይት ላይ ጥገኛ በሆኑት ዩናይትድ ስቴትስን ጨምሮ በሌሎችም አገራት ላይ ከፍተኛ ጫና ሊኖረው ይችላል።
የሆርሙዝ የባሕር ክፍል በኢራን እና በኦማን መካከል የሚገኝ መተላለፊያ ወሽመጥ ነው። መግቢያው እና መውጫው 50 ኪሎ ሜትር ስፋት ያለው ሲሆን፣ በመሃል ላይ ደግሞ በጣም ጠባብ የሆነው ቦታ 40 ኪሎ ሜትር ብቻ ነው።
ወሽመጡ በማዕከላዊው ክፍል ብቻ ትላልቅ መርከቦች ለማሳለፍ የሚሆን ጥልቀት አለው።
የባሕር አሳሾች መግቢያ እና መውጫው ለትልልቅ መርከቦች ደኅንነቱ የተጠበቀ መሆኑን ያረጋገጡ ሲሆን፣ በመካከልም ክብደት ያለውን ነዳጅ ጭነው ለሚጓዙ ምቹ መሆኑን ይገልጻሉ።
እነዚህ ግዙፍ መርከቦች ወደ 10 ኪሎ ሜትር ስፋት ባለው የሰርጡ ክፍል ላይ መቅዘፍ ይኖርባቸዋል።
ነዳጅ ጫኝ መርከቦች በፋርስ ባሕረ ሰላጤ ሲያልፉ በኢራን እና በአረብ አገራት መካከል አወዛጋቢ በሆኑት የቱንብ ደሴቶች አቅራቢያ ያልፋሉ።
በወሽመጡ ላይ የሚተላለፉ የንግድ መርከቦችን የሚያስተጓጉሉ ካሉ ወታደራዊ እርምጃ ከግምት እንደሚገባ ባለሙያዎች ይናገራሉ።
ይህ ደግሞ በአውሮፓውያኑ 1980 እስከ 1988 ድረስ በተካሄደው የኢራን እና የኢራቅ ጦርነት ወቅት ተከስቷል።
ዶናልድ ትራምፕ ከሦስት ሳምንት በላይ በዘለቀው የኢራን ጦርነት ምከንያት የተዘጋው ይህ ወሽመጥ እንዲከፈት የ48 ሰዓት የጊዜ ገደብ ሰጥተው ያ የማይሆን ከሆነ ግን የቴህራን የኃይል ማመንጫዎችን ለማውደም ዝተዋል።