ቀጥታ, የተኩስ አቁም ድርድሩ በተደናቀፈበት ሁኔታ አሜሪካ እና ኢራን ጥቃት መፈጸማቸውን አስታወቁ

የአሜሪካ ጦር በኢራን ደሴት ላይ ‘ራስን የመከላከል’ ጥቃት መፈጸሙን እና ወደ መርከቦች እና የባሕረ ሰላጤው አገራት የተተኮሱ ሚሳዔሎች እና ድሮኖችን መትቶ መጣሉን አስታወቀ። የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) በሆርሙዝ ወሽመጥ እና ኣለይ በቄሸም ደሴት ላይ “ኢራን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ አገራት ልትፈጽም የነበረውን የጥቃት ሙከራ ተከትሎ” ጥቃት መሰንዘሩን አስታውቋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. አሜሪካ የኢራን ግዙፍ የክሪፕቶ መገበያያ ከአብዮታዊ ዘቡ ጋር ግንኙነት አለው በሚል ማዕቀብ ጣለች

    አሜሪካ ማክሰኞ ዕለት የኢራን ግዙፍ የክሪፕቶከረንሲ መገበያያ የቴህራን መንግሥት እና ስማቸው በጥቁር መዝገብ ላይ የሰፈሩ ኩባንያዎች የምዕራባውያንን ማዕቀብ ለማለፍ ያገለግላል በሚል ማዕቀብ ጣለች።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል በግንቦት ወር ኖቢቴክስ (Nobitex) የሚባለው የክሪፕቶከረንሲ መገበያያ ከአገሪቱ ሕጋዊ የገንዘብ ሥርዓት ጋር በትይዩነት ለማዕከላዊ ባንኩ እና ለአብዮታዊ ዘቡ እያገለገለ መሆኑን በመጥቀስ ዘግቦ ነበር።

    ዘገባው አክሎም ኖቢቴክስ ኢንተርኔት በተዘጋበት ወቅትም አገልግሎት ሲሰጥ መቆየቱን አመልክቶ በሚሊዮን ዶላሮች የሚቆጠሩ ግብይቶችን ማካሄዱን አሳይቷል።

    የአሜሪካ ግምጃ ቤት ኃላፊ ስኮት ቤሴንት ማክሰኞ ዕለት ባወጡት መግለጫ “የኢራን ኢኮኖሚ እየተንኮታኮተ ባለበት ወቅት አገዛዙ ለራሱ እኩይ አጀንዳው የዲጂታል መገበያያዎችን ማዕቀብ ለማምለጥ እና ሃብት ከአገር ውጭ ለማሻገር መጠቀም መርጧል” ብለዋል።

    የሮይተርስ ዘገባ እንደሚያሳየው ኖቢቴክስ ከኢራናውያን ቤተሰቦች በተገኙ ወንድማማቾች የተመሠረተ ሲሆን፣ ከአዲሱ ጠቅላይ መሪ ጋር ጥብቅ ቁርኝት አላቸው።

    የአሜሪካ ግምጃ ቤት ሁለቱ ወንድማማቾች ላይ ማዕቀብ መጣሉን ማክሰኞ ዕለት አስታውቋል።

    ኖቢቴክስ ለኢራን መንግሥት “ጠንካራ ድጋፍ” እየሰጠ ነው፤ እንዲሁም ለአብዮታዊ ዘቡ እና ለአገሪቱ ማዕከላዊ ባንክ “በርካታ ቁጥር ያለው” የዲጂታል ግብይቶችን አመቻችቷል ብሏል።

    "በኢራን ውስጥ አሜሪካ ጦርነት መክፈቷን ተከትሎ ኖቢቴክስ የኢንተርኔት አገልግሎት ቢቋረጥም የአገዛዙን ሀብት ለመከላከል በኢራን ውስጥ ንብረቶችን እና ገንዘቦችን ለማንቀሳቀስ ሚና ተጫውቷል።"

  2. እስራኤል ከሄዝቦላህ ጋር ከፊል ተኩስ አቁም ከተስማማች በኋላ በደቡባዊ ሊባኖስ ጥቃቶችን ፈጸመች

    ኢራን ማክሰኞ ዕለት በደቡባዊ ሊባኖስ የምትፈጽመውን ጥቃት የቀጠለች ቢሆንም በኢራን ከሚደገፈው ሄዝቦላህ ጋር የደረሰችውን ከፊል ተኩስ አቁም ተከትሎ በዋና ከተማዋ ቤይሩት ላይ ጥቃት አለመፈጸሟን ተገለጸ።

    ሊባኖስ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ሰኞ አመሻሽ ላይ ይፋ ያደረጉትን ስምምነት ተከትሎ ሄዝቦላህ እስራኤል ላይ ጥቃት የማይፈጽም ከሆነ ጦሯ ቤይሩትን እንደማያጠቃ በማሳወቃቸው ድብዳው አልተፈጸመም ብላለች።

    ኢራን በበኩሏ እስራኤል በሊባኖስ ላይ ምትፈጽመው ጥቃት ከአሜሪካ ጋር ጦርነቱን ለማቆም የምታደርገውን ድርድር አደጋ ላይ የሚጥል መሆኑን አስታውቃለች።

    የተኩስ አቁሙ ይፋ ከሆነ በኋላ የእስራኤል ጦር ወደ አገሪቱ ሰሜናዊ ክፍል የተተኮሱ ተወንጫፊዎችን ማክሸፉን አስታውቋል።

    ሄዝቦላህ በደቡባዊ ሊባኖስ የሚገኙ የእስራኤል ኃይሎች ላይ ጥቃት መፈጸሙን የገለጸ ሲሆን፣ እስራኤል በበኩሏ ከባድ ጥቃት ማድረሷን አስታውቃለች።

    የሊባኖስ ጤና ሚኒስቴር እስራኤል በጃባል አመል ሆስፒታል አጠገብ የሚገን ሕንጻ ላይ ሰኞ ከሰዓት ጥቃት ከፈጸመች በኋላ አራት ሰዎች መገደላቸወን እና 127 መጎዳታቸውን አስታውቋል።

    ከተጎዱት መካከል 39 የሆስፒታል ሠራተኞች የሚገኙበት ሲሆን፣ አራቱ በአስጊ ሁኔታ ውስጥ ናቸው ተብሏል።

    የእስራኤል ጦር በአካባቢው የሚገኝ “የአሸባሪው ሄዝቦላህን መሠረተ ልማት” ማጥቃቱን ገልጾ፤ በሆስፒታሉ ላይ ጉዳት ቢደርስም “ዒላማ አልነበረም” ሲል አስተባብሏል።

    ሄዝቦላህ ሰላማዊ ሰዎች መሠረተ ልማቶች እና ሕዝብ በሚኖርባቸው ቦታዎች ላይ ይሸሸጋል ሲል ማስረጃ ሳያቀርብ ይወነጅላል።

    የሊባኖስ ጤና ሚኒስቴር በበኩሉ ባለፉት ሦስት ወራት ብቻ 128 የድንገተኛ አደጋ ሠራተኞች እና የጤና ባለሙያዎች መገደላቸውን በአምቡላንሶች እና በሕክምና ተቋማት ላይ ደግሞ 159 ጥቃቶች መፈጸማቸውን አስታውቋል።

    ሚኒስትሩ አክሎም ጦርነቱ ከተጀመረ ጊዜ አንስቶ 3,468 ሰዎች መገደላቸውነ የገለጸ ሲሆን፣ ቁጥሩን ግን ሰላማዊ ሰዎችን እና ተዋጊዎች አልለየም።

    የተባበሩት መንግሥታት በበኩሉ የእስራኤል ጦር ከአገሪቱ አንድ ስምንተኛ አካባቢ ነዋሪዎች ከመኖሪያቸው ለቅቀው እንዲወጡ ካስጠነቀቀ ወዲህ 1 ሚሊዮን ሰዎች መፈናቀላቸውን ገልጿል።

    እስራኤል 25 ወታደሮቿ እና አራት ሰላማዊ ሰዎች በዚህ ጦርነት ወቅት መገደላቸውን አስታውቃለች።

  3. የተኩስ አቁም ድርድሩ በተደናቀፈበት ሁኔታ አሜሪካ እና ኢራን ጥቃት መፈጸማቸውን አስታወቁ

    የአሜሪካ ጦር በኢራን ደሴት ላይ ‘ራስን የመከላከል’ ጥቃት መፈጸሙን እና ወደ መርከቦች እና የባሕረ ሰላጤው አገራት የተተኮሱ ሚሳዔሎች እና ድሮኖችን መትቶ መጣሉን አስታወቀ።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) በሆርሙዝ ወሽመጥ እና ኣለይ በቄሸም ደሴት ላይ “ኢራን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ አገራት ልትፈጽም የነበረውን የጥቃት ሙከራ ተከትሎ” ጥቃት መሰንዘሩን አስታውቋል።

    ኢራን ወደ ኩዌት ሁለት ሚሳዔሎችን ማስወንጨፏን ነገር ግን የታለመላቸውን ስፍራ ሳይደርሱ መውደቃቸውን እንዲሁም ሦስት ወደ ባሕሬን የተወነጨፉ ደግሞ በአየር ላይ እንዲከሽፉ መደረጋቸውን ገልጿል።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ በበኩሉ በቄሸም ደሴት በሚገኝ የግንኙነት ማማ ላይ ለተፈጸመ ጥቃት በሰጠው ምላሽ በቀጣናው የሚገኙ የአሜሪካ የጦር ሰፈሮችን እና ሂሊኮፕተሮችን ማጥቃቱን በአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን በኩል አስታውቋል።

    ሴንትኮም በቄሸም ደሴት ላይ የተፈጸመው ጥቃት የኢራን ጦር የምድር መቆጣጠሪያ ጣቢያ፣ ኢራን “በቀጣናው ውሃዎች ላይ የማለፍ መብት ያላቸው ሰላማዊ ባሕረተኞች” ላይ የተኮሰቻቸውን ሦስት ድሮኖችን መትቶ መጣሉን አስታውቋል።

    አብዮታዊ ዘቡ “የሆርሙዝ ወሽመጥን ደኅንነት ማወክ ጠብ አጫሪውን የአሜሪካ ጦር ከባድ ዋጋ ያስከፍለዋል” ሲል በመግለጫው ላይ አስታውቋል።

    ኢራን በተደጋጋሚ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች በሚገኙባቸው ባሕሬን እና ኩዌት ላይ ጥቃቶቸን ፈጽማለች።

    ቀደም ሲል ሴንቲኮም አሜሪካ የጣለችውን እገዳ ተከትሎ ወደ ኢራን እየቀዘፈ የነበረ ነዳጅ ጫኝ መርከብን ማጥቃቱን እና እንዳይንቀሳቀስ ማድረጉን አስታውቋል።

    የአሜሪካ አየር ኃይል የቦትስዋናን ሰንደቅ ዓላማ የሰቀለ ነዳጅ ጫኝ መርከብ በተደጋጋሚ የተሰጠውን ማስጠንቀቂያ ችላ ማለቱን ተከትሎ በሞተሩ ላይ ጥቃት መፈጸሙን ተገልጿል።

    ሴንቲኮም ማክሰኞ ዕለት መርከቦ ላይ ጥቃት ሲፈጽም የሚያሳይ ተንቀሳቃሽ ምሥል ያሠራጨ ሲሆን የኢራን ጦር በይፋ የሰጠው ምላሽ የለም።

    ዕዙ በመግለጫው ከአውሮፓውያኑ ሚያዝያ 13 ጀምሮ አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን ማገዷን አስታውሶ፣ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ 122 መርከቦች አቅጣጫቸውን አንዲቀይሩ እና እንዲመለሱ መደረጋቸውን አሻፈረኝ ያሉትም ሞተራቸው እነዳይሠራ መደረጉን አስታውቋል።

    ቢቢሲ የቦትስዋናን መንግሥት አስተያየት ለማግኘት ቢሞክርም አልተሳካም።

    አሜሪካ ይህንን ጥቃት የፈጸመችው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ማርኮ ሩቢዮ በአገሪቱ ምክር ቤት ለመጀመሪያ ጊዜ ቀርበው ስለ ኢራን ጦርነት ከተጠየቁ በኋላ ነው።

  4. ኢራን ሠራዊቷ መጠናከሩን ስትገልጽ፣ እስራኤል ደግሞ የኢራን መንግሥት መሠረቱ ተናግቷል አለች

    ኢራን የጦር ሠራዊቷ ከጦርነቱ በኋላ የበለጠ መጠናከሩን ስትገልጽ፣ እስራኤል ደግሞ የኢራን መንግሥት ክፉኛ ተዳክሞ ሊወድቅ መቃረቡን ጠቅላይ ሚኒስትሯ ተናገሩ።

    የኢራን ሠራዊት የተኩስ አቁም በተደረገበት ጊዜ በሁሉም መስኩ ለውጊያ ዝግጁ የሚያደርጉ ሥራዎችን ሲያከናውን መቆየቱን የአብዮታዊው ዘብ ቃል አቀባይ ገለጹ።

    ሁሴን ሞሄቢ እንደተናገሩት "በተኩስ አቁሙ ወቅት የሠራዊታችን ተልዕኮ የመፈጸም አቅም ጨምሯል፣ በተፈጠረው ዕድልም የውጊያ አቅሙ፣ ጥንካሬው፣ ዝግጁነቱ እና አደጋን የመቋቋም ብቃቱ ተጠናክሯል። በአሁኑ ወቅትም ጦሩ ቀደም ሲል ከነበረው አቋም በተሻላ ሁኔታ ላይ ይገኛል” ብለዋል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታኒያሁ የኢራን መንግሥት በደረሰበት ጥቃት መሠረቱ መናጋቱን እና መውደቁ የማይቀር መሆኑን በኤክስ ገጻቸው ላይ ጽፈዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ "የዚህ የሽብር አገዛዝ መሠረቱ ተናግቷል” በማለት “አገዛዙ ከዚህ በኋላ ቀድሞ ወደነበረበት ደረጃ ፈጽሞ አይመለስም፤ መውደቁ እንደማይቀር እነግራችኋለው” ሲሉ የኢራን መንግሥት መዳከሙን አመልክተዋል።

    የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ይህንን አስተያየት የሰጡት የኢራን ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሜኒ በተመሳሳይ እስራኤል ክፍኛ መዳከሟን ከተናገሩ በኋላ ነው።

    ጠቅላይ መሪው በቅርቡ ባስተላለፉት መልዕክት “አስራኤል መጪዎቹን 15 ዓመታት አታይም” በማለት ትጠፋለች የሚል አስተያየት ሰንዝረዋል።

    እስራኤል በኢራን ላይ ሁለት ጊዜ ጥቃቶችን የፈጸመች ሲሆን፣ ኢራን በበኩሏ ከባድ የአጸፋ ምላሽ በሚሳዔሎች እና በድሮኖች ፈጽማለች።

    ባለፈው የካቲት እስራኤል ከአሜሪካ ጋር አብራ በኢራን ላይ በፈጸመችው ጥቃት የኢራን ጠቅላይ መሪን ጨምሮ በርካታ የአገሪቱ ባለሥልጣናት ተገድለዋል።

    ኢራንም በበኩሏ በእስራኤል እና በአካባቢው ባሉ የአሜሪካ አጋሮች ላይ ተከታታይ የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃቶችን በመፈጸም ከባድ ጉዳትን አድርሳለች።

  5. ፕሬዝዳንት ሩቶ በአሜሪካ የሚቋቋመውን የኢቦላ ህክምና ማዕከልን ሲደግፉ ፍርድ ቤት ዕግዱን አራዘመ

    የኬንያው ፕሬዝዳንት ዊሊያም ሩቶ ተቃውሞ የገጠመውን የኢቦላ ተጠርጣሪዎችን ለመለየት የሚያስችል ማዕከል ለማቋቋም ከአሜሪካ ጋር የተደረሰውን ስምምነት ቢደግፉም የአገራቸው ፍርድ ቤት ግን በማዕከሉ ላይ የጣለውን ዕገዳ አራዘመ።

    ላይኪፒያ በተባለችው የኬንያ ማዕከላዊ ግዛት ውስጥ የሚከፈተውን የህክምና ማዕከል በመቃወም ከተካሄደው ሰልፍ ጋር በተያያዘ ሁለት ሰዎች መገደላቸው ተዘግቧል።

    ፕሬዝዳንቱ ከአሜሪካ ጋር የሚቋቋመው የህክምና ማዕከል ኬንያውያንን ጭምር የሚጠቅም የጋራ ስምምነታቸው አካል መሆኑን እና ኬንያ ተላላፊ በሽታዎችን ለመከላከል እንዲሁም ህሙማንን ለማከም የሚያስችላት መሆኑን በመጥቀስ ተከራክረዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ይህንን በተናገሩበት ጊዜ የኬንያ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ከአሜሪካ እና ከሌላ ከማንኛውም የውጭ መንግሥት ጋር በሚደረግ ስምምነት የሚመሠረት እና ሥራ ላይ የሚውል የኢቦላ ህሙማን መለያ ተቋምን የሚያግደውን ጊዜያዊ ውሳኔውን አራዝሟል።

    ፍርድ ቤቱ ዛሬ ባስተላለፈው ውሳኔ የኬንያ መንግሥት በሰባት ቀናት ውስጥ ከአሜሪካ መንግሥት ጋር የተደረሰውን አወዛጋቢ ስምምነት ይፋ እንዲያደርግ አዝዟል።

    በተጨማሪም መንግሥት እና ሌሎች አካላት “ጉዳዩ በፍርድ ቤት እልባት እስኪያገኝ ድረስ የኢቦላ ለይቶ ማቆያ ማዕከል ከመክፈት፣ ሥራ ከማስጀመር፣ ፈቃድ ከመስጠት እና ከማጽደቅ እንዲታቀቡ” ውሳኔውን አጽንቷል።

    የለይቶ ማቆያ ማዕከሉ ይቋቋምበታል በተባለው በማዕከላዊ ኬንያ ናኙኪ ከተማዋ ውስጥ ውጥረት የተፈጠረ ሲሆን፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎች የህክምና ማዕከሉ ሊያስከትል የሚችለውን ተጽእኖ በመጥቀስ አደባባይ ወጥተው ተቃውሟቸውን ገልጸዋል።

    በተቃዋሚዎች እና በፖሊስ መካከል በተፈጠረው ግጭት ሁለት ሰዎች በጥይት ተመትተው መሞታቸው ተዘግቧል።

  6. ተመድ እስራኤል የሊባኖስን አምባ መቆጣጠሯን በተመለከተ አስቸኳይ ውይይት አካሄደ

    የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት እስራኤል የሊባኖስን ጥንታዊ አምባ - ቢውፎርትን በቁጥጥር ሥር ማዋሏን በተመለከተ ትናንት አስቸኳይ ውይይት አካሄደ።

    በተመድ የሩሲያ አምባሳደር ቫስሊ ነቤንዝ “እስራኤል እና ሊባኖስ በአሜሪካ አሸማጋይነት የደረሱት የተኩስ አቁም ስምምነት እስራኤል ሊባኖስ ላይ ጥቃት እንድትፈጽም ከለላ ሰጥቷል” ብለዋል። ሊባኖስ የጋዛ ሰርጥ እጣ ፈንታ እንደሚጠብቃትም አክለዋል።

    በተመድ የፈረንሳይ ልዑክ ጀሮም ቦንፎን ውይይቱ እንዲካሄድ አገራቸው ጥሪ ማቅረቧን ጠቅሰው “እስራኤል ራሷን የመለካከል መብት ቢኖራትም ሊባኖስ ላይ የምታደርሰው ጥቃት ምክንያታዊ አይደለም” ብለው ንግግር አድርገዋል።

    በሺዎች የሚቆጠሩ ንጹኃን እንደተጎዱ እና እንደተፈናቀሉ የፈረንሳዩ ተወካይ ተናግረዋል።

    የአሜሪካ ተወካይ ማይክል ጄ ዋልዝ በበኩላቸው፤ድርድርን ጨምሮ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች መቀጠላቸውን ገልጸዋል።

    “ሕጋዊው የሊባኖስ መንግሥት በቴህራን ከሚደገፈው አሸባሪ አገሪቱን ነጻ ለማውጣት ተነሳሽነት አሳይቷል” ብለዋል።

    የሊባኖስ ተዋካይ አሕመድ አራፋ ደግሞ መንግሥታቸው ነገሮችን ለመቆጣጠር ቢሞክርም “እስራኤል እንደ ሁልጊዜው ቀጣናዊውን ሁኔታ እየተጠቀመችበት ነው” ብለዋል።

    እስራኤል ሐኪሞችን፣ ሆስፒታሎችን፣ ጋዜጠኞችን፣ ትምህርት ቤቶችን እና የፀጥታ ተቋማትን ዒላማ በማድረግ “ስልታዊ የውድመት ዘመቻ” መክፈቷንም ጠቅሰዋል።

    በተመድ የእስራኤል ልዑክ ዳኒ ዳኖን “አንድ ቀን ተነስተን ሊባኖስ ለመግባት አልወሰንም። አማራጭ አጥተን ነው” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።

    ኢራን ሄዝቦላህን በእጅ አዙር መጠቀም መቀጠሏን ጠቅሰው፤ የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ ቢደረስም “ሄዝቦላህ ሚሳዔል እና ድሮን መተኮስ” እንዳላቆመ ተናግረዋል።

  7. በቀጣይ ሳምንት ከኢራን ጋር ስምምነት ላይ ሊደረስ እንደሚችል ትራምፕ ተናገሩ

    ከኢራን ጋር የተኩስ አቁም ለማራዘም እና የሆርሙዝ ወሽመጥን ለመክፈት በቀጣይ ሳምንት ስምምነት ላይ እንደሚደረስ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለኤቢሲ በሰጡት ቃለ ምልልስ ተናገሩ።

    “አሁን ላይ ነገሮች በጣም ጥሩ ናቸው። ውስን ችግር ነበር፤ ነገር ግን እንዳያችሁት በፍጥነት ፈትቼዋለሁ” ሲሉ በስልክ በሰጡት ቃለ ምልልስ ገልጸዋል።

    ትራምፕ ችግር ብለው የጠቀሱት እስራኤል በሊባኖስ ላይ የምታደርሰው ጥቃት ኢራንን ማስቆጣቱን ነው።

    ሄዝቦላህ በእስራኤል ላይ ጥቃት ማድረስ እንዲያቆም ከአሜሪካ የቀረበለትን ሐሳብ መቀበሉን ሊባኖስ አስታውቃለች። እስራኤልም በሊባኖስ መዲና ቤሩት ጥቃት ላለመፈጸም መስማማቷም ተገልጿል።

    ትራምፕ ከጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ እና ከሄዝቦላህ ተወካዮች ጋር መወያየታቸውን ጠቅሰው “ተኩስ ለማቆም ተስማምተዋል” ብለዋል።

    ትራምፕ “ሄዝቦላህን አትተኩሱ ብያቸዋለሁ። ቢቢ [ኔታንያሁ] እንዳይተኩስም ነግሬዋለሁ። ሁለቱም ተኩስ አቁመዋል” ሲሉም አክለዋል።

    በቀጣይ ሳምንት የሆርሙዝ ወሽመጥ ይከፈታል ብለው እንደሚያምኑም ፕሬዝዳንቱ ተናግረዋል።

  8. ሩሲያ በዩክሬን ከተሞች በፈጸመችው ጥቃት ቢያንስ 16 ሰዎች ተገደሉ

    ሩሲያ በዩክሬን ዋና ዋና ከተሞች ባደረሰችው ጥቃት ቢያንስ 16 ሰዎች እንደተገደሉ እና ብዙዎች እንደቆሰሉ ተገለጸ።

    በዲፕሮ ከተማ 11 ሰዎች ሲገደሉ 25 ሰዎች ተጎድተዋል። ዛሬ ንጋት ላይ በደረሱ ጥቃቶች በመዲናዋ ኪቭ አምስት ሰዎች መገደላቸው እና 51 መቁሰላቸውም ተዘግቧል፤ 35 ያህሉ ደግሞ ሆስፒታል ገብተዋል።

    የኪቭ ከንቲባ ቪታሊ ክሊሽኮ እንዳሉት ሁለት ግዙፍ የመኖሪያ ሕንጻዎች የተመቱ ሲሆን፤ ሰዎች በፍርስራሽ ሥር ተቀብረው ሊሆን እንደሚችል ይገመታል።

    ዩክሬን ባለፈው ወር የድሮን ድብደባ በመፈጸሟ በምላሹ “ስልታዊ ጥቃት” ለማድረስ ሞስኮ ስትዝት ቆይታለች።

    ሩሲያ በቁጥጥሯ ሥር ባዋለችው የዩክሬን ሉሀንስክ ግዛት በደረሰው የድሮን ጥቃት 21 ሰዎች ተገድለዋል።

    የኪቭ ከንቲባ ነዋሪዎች ከቤታቸው እንዳይወጡ ማስጠንቀቂያ ሰጥተዋል። “ጠላታችን በባለስቲክ ሚሳዔል ጥቃት እየፈጸመ ነው” ሲሉም ተናግረዋል።

    በአብዛኞቹ የዩክሬን ከተሞች የአየር ጥቃት ማስጠንቀቂያ ደወሎች እየተሰሙ ነው። በማዕከላዊ ኪቭ ጭስ መታየቱም ተገልጿል።

    በሌላ በኩል በሩሲያ ኢልስኪ የነዳጅ ማቀነባበሪያ የደረሰ ጥቃት እሳት ማስነሳቱ ተገልጿል።

    ኪቭ ውስጥ የበርካታ ድሮኖች እና ፍንዳታ ድምጽ እየተሰማ ይገኛል። ሞስኮ የፈጸመችው ጥቃት በነዳጅ ማደያ እሳት አቀጣጥሏል።

  9. ሄዝቦላህ በእስራኤል ላይ ጥቃት ማድረሱን ለማቆም መስማማቱን ሊባኖስ ገለጸች

    ሄዝቦላህ በእስራኤል ላይ ጥቃት ማድረስ እንዲያቆም ከአሜሪካ የቀረበለትን ሐሳብ መቀበሉን ሊባኖስ አስታወቀች።

    እስራኤልም በሊባኖስ መዲና ቤሩት ጥቃት ላለመፈጸም መስማማቷም ተገልጿል።

    አሜሪካ የሚገኘው የሊባኖስ ኤምባሲ “አሜሪካ ሁለቱም ወገኖች ጥቃት እንዳያደርሱ ያቀረበችውን ምክረ ሐሳብ ሄዝቦላህ ተቀብሏል” ብሏል።

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁም ስምምነት ላይ መደረሱን አረጋግጠዋል።

    ሆኖም “ሄዝቦላህ ከተሞቻችን እና ዜጎቻችን ላይ ጥቃት ከፈጸመ ግን ቤሩትን እንደበድባለን” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኔታንያሁ እና ከሄዝቦላህ ተወካዮች ጋር መወያየታቸውን ጠቅሰው “ተኩስ ለማቆም ተስማምተዋል” ብለዋል።

    እስራኤል በሊባኖስ የምታደርሰው ጥቃት የኢራን እና አሜሪካን የተኩስ አቁም ስጋት ውስጥ እንደሚጥል ቴህራን መግለጿ ይታወሳል።

    የሊባኖስ ኤምባሲ ባወጣው መግለጫ “ሄዝቦላህ እስራኤል ላይ ጥቃት ካልፈጸመ እስራኤልም በቤሩት ጥቃት እንደማታደርስ ተስማምተናል” ብሏል።

    የተኩስ አቁሙ በሒደት “ሌሎች የሊባኖስ አካባቢዎችን እንደሚሸፍን” ተገልጿል።

    ኔታንያሁ በበኩላቸው “የእስራኤል መከላከያ ኃይል በታቀደው መሠረት በደቡብ ሊባኖስ ዘመቻውን ይቀጥላል” ብለዋል።

    ሁለቱ ወገኖች ተኩስ ለማቆም መስማማታቸውን ትራምፕ ከገለጹ በኋላ የተወሰኑ ግጭቶች መነሳታቸው ተዘግቧል።

  10. ፕሬዝዳንት ትራምፕ የአሜሪካ እና የኢራን ስምምነትን ለማረም ፍላጎት እንዳላቸው ተነገረ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከሦት ወራት በፊት የተጀመረውን የአሜሪካ እና ኢራን ጦርነት ለመቋጨት የሚያስችለውን ስምምነት ለማስተካከል ፍላጎት እንዳላቸው የዋሽንግተን መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    ለውጦቹ በሆርሙዝ ወሽመጥ እና የተብላላ የዩራኒየም አወጋገድ ጋር የተያያዙ እንደሆኑ በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ኒውስ ዘግቧል።

    ዋይት ሐውስ አስተያየት እንዲሰጥ ቢጠየቅም ምላሽ አልሰጠም።

    የኢራን ዋና ተደራዳሪ መሐመድ ባገር ጋሊባፍ እሑድ ዕለት የኢራን መብት ሙሉ ለሙሉ እስካልተጠበቀ ድረስ ቴህራን ምንም ዓይነት ስምምነት አትፈጽምም ብለዋል።

    የተኩስ አቁም ስምምነቱን ለማራዘም በሚያስችለው ማዕቀፍ ላይ ፕሬዝዳንት ትራምፕ እና ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጋር አርብ ዕለት ለንግግር ቢቀመጡም፤ ስብሰባው ቀጣይ እርምጃዎች ላይ ግልፅነት ሳይኖረው ተጠናቋል። ሙሉውን እዚህ ያንብቡ ፕሬዝዳንት ትራምፕ የአሜሪካ እና የኢራን ስምምነትን ለማረም ፍላጎት እንዳላቸው ተነገረ